Monday, February 11, 2019

መግባባት ይኖረን ዘንድ ምን እናድርግ? ምንስ እንሁን?

ከዐርባ አምስት (45) ዓመታት ቀደም ብሎ የጀመረው በሐገራዊ ጉዳዮቻችን ላይ የጋራ አቋም መያዝን ሽሽት ዛሬ ላይ የመጨረሻው ጫፍ ላይ ደርሷል። የአንድ ሐገር ሰዎች ተብለን እንጠራ እንጅ እርስ በእርስ የምንተያየው እንደተለያዩ ሐገራት ዜጎች ነው። እንደተለያዩ ሐገራት ብቻም ሳይሆን ታሪካዊ ጠላትነት እንዳላቸው ሐገራት ዜጎች መተያየት ከጀመርን ውለን አድረናል።

ኢትዮጵያ የሚለውን ሥም በጋራ እንጠራበት እንጂ ኢትዮጵያዊነትን በተመለከተ የምንጋራው አቋም የለንም። በአንድ ሐገር እየኖርን፣ አንድ የይለፍ ወረቀት (Pass Port) እየተጠቀምን፣ በአንድ መንግሥት ሥር እየተዳደርን፣ ወዘተ ... የጋራችን የምንለው እና የምንስማማበት ጉዳይ ግን የለንም። 

ይኸንን ከላይ ያነሳሁትን ነጥብ የሚያስረግጡ ብዙ ማሳያዎችን ማቅረብ ይቻላል። በርካታ የጥቁር ሕዝብ ሐገራትና ሕዝባቸው የነጻነት ፋና ወጊ አድርገው የሚያዩትን እና እንደድላቸው አድርገው የሚቆጥሩትን የዓድዋ ድል እንኳን ልንስማማበት አልቻልንም። የእነ እከሌ ድል ነው፤ የእኛ ጉዳይ አይደለም፤ ... ዓይነት የውርክብ ሐሳቦችን እየተወራወርን መናቆሪያ አድርገነዋል። ያለፈውን የኛው ታሪክ ከምንማርበት ይልቅ መበሻሸቂያ፣ መነቋቆሪያ፣ መነታረኪያ እነና የጥል ግንብ ማቆሚያ በማድረግ ላለመግባባት ስንኳትን እንውላለን።

ቋንቋን ከመግባቢያነትና ከሐሳብ መግለጫነት ነጥለን የጥልና የብጥብጥ መሣሪያ አድርገነዋል። በቋንቆቻችን ውስጥ የተከማቹ እውቀቶችን በመጋራትና በማጋራት የበሰለ ሐገራዊ አመለካከት ያለው ማኅበረሰብ ከመገንባት ይልቅ የመለያያ አጥር እየሠራንባቸው አቅጣጫው ወዳልታወቀ አድራሻ እየነጎድን ነው።  በቋንቆቻችን ውስጥ የተቀበሩ እውቀቶችን እያወጣን የጋራ የሚባል ማንነት ለመሥራት ከመጣር ይልቅ ልጆቻችን እና ታናናሾቻችን የማይግባቡበትን መንገድ ለመፍጠር የእነገሌን ቋንቋ ማወቅ የለባችሁም በማለት በእንቁላል ውስጥ እንዳለ ሽል አፍነን ለማስቀረት እንታትራለን። 

በዚህ ሁሉ ጉዟችን መግባባት የማይችል ዜጋ ለመፍጠር ተሳክቶልናል። ከተጣባን የችጋር ደከከን የሚያላቅቀን መንገድ መፈለግን ደግሞ በሚያስደምም ሁኔታ ረስተነዋል። የሰው ልጅ ያለውን በነጻነት የመሰብና የመሥራት ተፈጥሯዊ ሥጦታ በመንጠቅ ሲዋጣልን ራሳችንንም ሆነ ማኅበረሰባችንን የሚለውጥና ከድህነት አረንቋ የመምዘዣ መንገድ ለመቀየስ ግን ወገቡን እንደተመታ እባብ እየተቅመደመድን  ነው።

ለመሆኑ እንደዚህ የሆንነው ለምንድን ነው? ከዚህ የሐሳብ ድርቅና ቆፈንስ መውጣት የምንችለው እንዴትና በምን ዓይነት መንገድ ነው? መውጫ መንገዱን ለመፈለግስ ምን ማድረግና መሆን ይጠበቅብናል? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎች እያነሳን መወያየትና መሟገት አስፈላጊ ቢሆንም ረስተናቸዋል። በመሆኑም እንደግለሰብ የሚታየኝና የሚሰማኝን በዚኽች ጦማር በተከታታይ ለማቅረብ በመሞከር የድርሻየን ለመወጣት ጀምሬያለሁ። መግቢያው ይኼው። ቀጣዮቹ ክፍሎችም ይቀጥላሉ።

Tuesday, January 29, 2019

የዘንበል ዘንበል ጉዞ የት ያደርሰናል?

የኢትዮጵያን ታሪክ ስናነብም ሆነ እንደየዕድሜያችን መጠን የኢትዮጵያ ሕዝብ ለአገዛዝ እና ለገዥዎች የነበረውንና ያለውን ዕይታና አቀባበል መረዳት ከባድ አይሆንብንም። እኔም ባነበብሁት መጠንና በሕይወት ጉዞየ በታዘብሁት መጠን ጉዳዩን የቻልሁትን ያህል ለመረዳት ጥሬያለሁ። በኔ መረዳት መሠረት የኢትዮጵያ ሕዝብ እንደሕዝብ የአገዛዝ ሥርዓትና ገዥዎችን በተመለከተ የነበረውና ያለው አቋም "ዘንበል-ዘንበል" ተብሎ ሊገለጽ የሚችል ነው።

ዘንበል-ዘንበል ማለት ነፋስ በሚነፍስ ወቅት የነፋሱን አቅጣጫ ተከትሎ ጎንበስ ማለትን፤ እንደገናም ደግሞ ነፋሱ አቅጣጫ ቀይሮ ሲመጣ ወደተቀየረው አቅጣጫ ማጎንበስ ነው። ይህ በተፈጥሯቸው ጠንካራ ያልሆኑ የሣር ዝርያዎች ባሕሪ ነው። ሣሮች ከመነቃቀል የሚድኑት የነፋሱን አቅጣጫ ተከትለው በመተኛት ነው።

የኢትዮጵያ ሕዝብም የሣሮችን ተፈጥሯዊ ባሕሪ በመኮረጅ ከራሱ ጋር አላምዶና አዋድዶ የመጣው አገዛዝና ገዥ የያዘውን አቋም ተከትሎ እየተጓዘ የኖረና እየተጓዘም ያለ ነው። ከዚህ ባሕሪ ጋር መስማማቱንም "እንደንፋሱ አጎንብሱ" በሚል ምሳሌያዊ አነጋገር አስደግፎ የሕይወት መመሪያ እንዲሆን በማድረጉም የቀደሙትን ተከትሎ የሚመጣ አዲስ ትውልድ አገዛዝና ገዥዎችን በአዲስ መንገድ የሚያይበት መንገድ እንዳይቀርጽ ቀይዶ ይዞታል።

ዘንበል-ዘንበሉ ከሥርዓትም በላይ ግለሰብን ተመርኩዞ የተገነባ በመሆኑም አንድ ገዥ በተለየ መንገድ ሊመለክ ምንም አልቀረው እስኪባል ድረስ ለግለሰቡ ማጎብደድን ያስተማረና እያስተማረ ያለ ባሕሪ እንዲሆን አድርጎታል። በዚህም ምክንያት እንደ እንስሳ መንጋ ከፊት የቀደመው ገዥ የቀደደውን ቦይ ተከትሎ የሚፈስስ ኢ-ምክያታዊና ኢ-ተጠየቃዊ ግብስብስ አድርጎት አልፏል፤ እያለፈም ነው።

በዚህም ምክንያት ሥርዓት ገንብቶ የሚመጡ ገዥዎችን ሁሉ መምራትና መዘወር የሚያስችል መንገድ መቀየስ እንዳይቻል ሆኗል። በዚህም ምክንያት ሥልጣን የጨበጠውን ገዥ ባሕሪ ተከትለን የምንተምም ደመ-ነፍሳዊ መንጋ ሆነናል። የመጣው ሁሉ የቀደደልንን ቦይ ተከትለን የምንፈስ አስተውሎት የተሳነን ጥርቅሞች ሆነናል። የተለየ ዕይታ ያላቸውን የምንደቁስ፣ አንስተን እያፈረጥን ከመሬት የምንሰፋ ባለትንፋሽ ግዑዞችም ሆነናል።

የዘንበል-ዘንበል ጉዟችን ድንብርብር እና በፍርሃት ቆፈን የተሸበብን፣ ከሥርዓት ግንባታ ይልቅ ግለሰባዊ ማንነት ላይ የምንንጠለጠል የጅምላ አስተሳሰብ ተጠቂ አድርጎናል። ሆኖም ግን ቀጥለንበታል። ዛሬም ከተቀደደልን ቦይ ባሻገር የማናይ አቅመ-ቢስ መንታሎች አድርጎናል። ራሳችንን በራሳችን የምናፍን ገራሚ ፍጡሮች አድርጎናል።

ሆኖም ዘንበል-ዘንበላችንን ለማቆም አልቻልንም፤ ወይም ለማቆም ፍላጎቱም ሆነ ፈቃዱ የለንም። ቀጥለንበታል። የት እንደሚያደርሰን ግን አናስብም። ግን ለመሆኑ ይህ የዘንበል-ዘንበል ጉዟችን የት ያደርሰናል?

Monday, October 8, 2018

ወዴት ዘመም ዘመም!


አቶ ልደቱ አያሌው ከዋልታ ቴሌቪዥን ጋር ያደረጉት የሁለት ክፍል ቆይታ ተመለከትኩት፡፡ ሆኖም ግን ከቆይታቸው የተረዳሁት ነገር እስከዛሬ የሚነገርባቸውን የሚያጠናክርልኝ እንጂ ንጹህነታቸውን የሚያሳይ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ በተደጋጋሚ የሚያቀርቧቸው ክስ እንበላቸው ወቀሳዎች እርስ በርሳቸው የሚጣረሱ ናቸው፡፡ አንዴ የተሻልሁ ፖለቲከኛ በመሆኔና በምክንያትነቴ ተገለልኩ፤ ሐሰተኛ ውንጀላ ተበራከተብኝ ሲሉ ቆይተው ሌላ ጊዜ ደግሞ በማንነቴ የፓርቲ ስልጣን እንዳላገኝ ተደረግሁ፣ የሻጥር ዘመቻ ተዘመተብኝ ይላሉ፡፡ በማንነቴ ሲሉም ዐማራ በመሆኔ ማለታቸው ይመስለኛል፡፡

ዐማራ በመሀኔ መገለል ደረሰብኝ የሚሉት ሰው ግን ለዐማራ ሕዝብ መብት ለመከራከር ከተቋቋመው መ.ዐ.ሕ.ድ አፈንግጠው ወጥተው የራሳቸውን ድርጅት የመሠረቱትና በፖለቲካ ውስጥ በነበሩባቸው ከ20 በላይ ዓመታት ውስጥ ዐማራው ፍዳውን ሲያይ ድምጻቸውን አጥፍተው ሲመለከቱ እና አንዳንዴም በአደባባይ ሲያሽቃብጡ ይታዩ የነበሩት ሰውዬ መሆናቸው ይገርማል፡፡ ታዲያ በማንነታቸው የሚናገሩት ሁሉ ከደረሰባቸው እስከዚህ ጊዜ ድረስ ምን አስጠበቃቸው? ለምንድን ነው ባለፉት 13 ዓመታት ውስጥ ትንፍሽ አላሉም? ስንቶቹ ዐማራ በመሆናቸው ብቻ ብዙ ስቃዮችን ሲሰቃዩ ድምጻቸውን አጥፍተው ጎሬ ውስጥ ተወሽቀው የኖሩት? ዛሬስ ድንገት ዐማራ በመሆኔ ተበድያለሁ ላመለት የሚያበቃቸው ምን ነገር አገኙ? ነው ወይስ ከአቶ መለስ ጀምሮ ሲለለምኑኝ ነበር ያሉትን ጥያቄ ተቀብለው የቀድሞው ብ.አ.ዴ.ን (የዛሬው አ.ዴ.ፓ) አባል ለመሆን ወሰኑ? ወይስ አ.ብ.ንን (የዐማራ ብሔርተኝነት ንቅናቄ) ለመቀላለቀል ዕድሉን አገኙ? ይህ ሆኖ ከሆነ ሰውዬው በሕይቀት ዘመናቸው ዐራተኛ ፓርቲያቸውን ተቀላቅለው የማውደም ዓላማቸውን ለማሳካት እየቋመጡ ያሉ ይመስለኛል፡፡

Sunday, October 7, 2018

ወይ ሕመም!

የሳምንቱ መጨረሻ ቀናት የመንደራችን ሙግት "ትጥቅ መፍታት እና አለመፍታት" ላይ አትኩሯል። የተለያዩ አተያዮች እና አቋሞችም እየተንጸባረቁበት ነው። ሆኖም ግን ለሙግት ማሳመኛነት እየተነሱ ካሉ አመክንዮዎች አንዱ ግን አሳማኝ ካለመሆኑም በላይ የሐሳቡን አቀንቃኞች የኢትዮጵያን ባሕል አለማወቅ ወይም እያወቁ መካዳቸውን የሚያመለክት ሆኖ አግኝቸዋለሁ።
የመሳሪያ ባለቤት መሆን በየትኛውም የሐገራችን የገጠር ማኅበረሰብ የኩራት ምንጭና የአንድ ወንድ ሙሉ ሰውነት ማረጋገጫ ተደርጎ የሚወሰድ ነው። ከአርብቶ አደሩ እስከ አርሶ አደሩ መሳሪያ መያዝን የባሕሉ አንድ አካል አድርጎ ከመውሰዱም በላይ የመከበር ምልክቱም አድርጎ ይወስደዋል። በመሆኑም የመሳሪያ ባለቤት መሆን የማይፈልግ ኢትዮጵያዊ አርሶ አደር ወይም አርብቶ አደር ያለ አይመስለኝም።
ስለሆነም መሳሪያን ከቤተሰቡ እንደ አንዱ ለዚያውም የብረት መዝጊያ ተብሎ እንደሚቆጠረው አድርጎ የሚወስደውን ኢትዮጵያዊ የገጠረ ነዋሪ መሳሪያህን አስረክብ ወይም ትጥቅ ፍታ ብሎ መጠየቅ የባሕሉን አንድ ጎን እርሳው የማለት ያህል የሚከብደው ነው። እንደውርደት የሚቆጠርና አስነዋሪ ተግባር እንደተፈጸመበት የሚያየውም ነው። መሳሪያ የሌለው ሌጣ መሆኑም ባሕሉ የሰጠውን የወንድነት ሚና አሳጥቶ እንደሴት የሚያስቆጥረውና በማኅበረሰቡ ዘንድም እንደፈሪና ሰነፍ የሚያስቆጥረው ነው።
ይሁን እንጅ ይህንን የማኅበረሰብ ክፍል መሳሪውን እንዲያስረክብና ትጥቅ እንዲፈታ አላደርግም የሚል ሐሳብን የተደራጀ ቡድንን ትጥቅ አላስፈታም ከሚል ሐሳብ እያነጻጸሩ ምክንያታዊ እና ትክክለኛ አስመስሎ ለማቅረብ የሚውተፈተፉ ሰዎች እየታዩ ነው። ይህም የሐገራችን ሕዝብ የገጠሩ ክፍል ማኅበረሰብ እንደመግለጫው ወስዶ የባሕሉ አካል ያደረገውን የመሳሪ ባለቤትነት ልማድ አኮስሶ የአንድ ቡድን መገለጫ ለማድረግ ከመሯሯጥ የሚተናነስ አይደለም። ለማኅበረሰብ መገለጫዎች ንቀት ከማሳየት በላይም ሽፍትነትን ማበረታታት ነው። ሰፋ ሲልም የጎሰኝነት እና የጎጠኝነት አስተሳሰብ የወለደውን እኩይ ባሕርይ እውናዊ እና ቅቡልነት ያለው አድርጎ ለማቅረብ መጣር ነው።
#እንደዚህ ዓይነት ንጽጽሮችን ትልቅ ከሚባሉ ስዎች ሲወጣ ማየትና መስማት ደግሞ ያማል።

Thursday, October 4, 2018

ጠያቂዋም ተጠያቂውም ሥሙን እየጠሩት ያልተገለጠው የዐማራው የሕልውና ፈተና፡-


የLTV Show አዘጋጅ ቤተልሔም ታፈሰ እና የአ.ብ.ን ሊቀ መንበር ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ ያደረጉትን ሙግት መሰል ውይይት በጥሞና አዳመጥሁት፡፡ የዐማራው ማኅበረሰብ የሕልውና ፈተና ገጥሞታል የሚለው የንቅናቄው አቋም የተመላለሱት ጉዳይ ግልጽ ሊሆንልኝ አልቻለም፡፡ ጋዜጠኛዋ ትንኮሳ ትላለች፤ ሊቀ መንበሩ ደግሞ የህልውና ፈተና ይላሉ፡፡ የሕልውና ፈተና መሆኑን ለማስረዳት ብዙ ማስረጃዎችን መጥቀስ ይችሉ የነበረ ቢሆንም ረግጦ የማስረዳት ክፍተት አስተውየባቸዋለሁ፡፡ ጋዜጠኛዋም በበኩሏ የሕዝብ ቁጥር ብዛትን እየጠቀሰች ያህን ያህል ስፋት ያለው ማኅበረሰብ እንዴት የሕልውና ፈተና አለበት ሊባል ይችላል እያለች ትሞግታለች፡፡ ይህ ሁሉ አስፈላጊ ነበር ወይ የሚለው እንዳለ ሆኖ የሕልውና ፈተና ተጋርጦበታል ለሚለው ጉዳይ የሚከተሉትን አስረጂዎች ማየት ይቻላል፡፡
በዐማራው ሕዝብ ላይ የተጋረጠውን የህልውና አደጋ ተጋርጦበታል ሲባል፡-
1.  ዐማራው በተለያዩ ክልሎች ውስጥ ላለፉት ሠላሳ ዓመታት በጅምላ ሲገደል፣ ቤት ተዘግቶበት ሲቃጠል፣ ሲፋናቀልና ከርስቱ ሲነቀል የቆየ መሆኑ፤ አሁንም እነዚህ ጉዳዮች እየተፈጸሙ መሆናቸው፣
2.  የቤተሰብ ምጣኔን እንደሽፋን የዐማራ ወጣቶች መውለድ እንዳይችሉ የማድረግ ሥራዎች እየተሠሩ መሆናቸው፣
3.  ወንጀል ሳይኖርባቸው ዐማራ መሆናቸውና መብታቸውን በመጠየቃቸው ብቻ በየማጎሪያ ቤቱ እየሰበሰቡ እንዳይወልድ የማኮላሸት ሥራ እየተሠራበት መሆኑ፣
4.  የመንግሥት ሥርዓትን ከሚመሩ ድርጅቶች ጀምሮ በሐገሪቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች ዐማራን ጠላትና ጨቋኝ አድርጎ የመተረክና ይህንንም ለማስረጽ በተለያዩ መንገዶች እየተሠራ መሆኑ፣
5.  በኢኮኖሚ ሥርዓቱ ግፉእ እንዲሆን የማድረድ ተግባር በፖሊሲ ደረጃ ተቀርፆ የሚሠራበት መሆኑ፣
6.  ዐማራው በሐገሩ ማግኘት የሚገባውን ማግኘት እንዳይችል፤ ከማይምነት እንዳይላቀቅና በድኅነት ሲማቅቅ እንዲኖር እየተሠራበት መሆኑ፣
7.  በተለይም ጋዜጠኛዋ ራሷ የመከራከሪያ ነጥብ አድርጋ ለማሳመኛነት ያቀረበችው ጉዳይ ዐማራው ምን ያህል የህልውና ፈተና የገጠመው እንደሆነ ለማሳያነት የሚቀርብ እንጂ እሷ እንዳለችው የሕልውና ፈተና የሌለበት መሆኑን ሊያሳይ የሚችል አይደለም፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የዐማራውን ያህል በሥፋትና በከፍተኛ ሁኔታ ተሠራጭቶ የሚኖር ሌላ ማኅበረሰብ የለም፡፡ በየትኛውም የሀገሪቷ አካባቢዎች በጣም በርካታ ቁጥር ያላቸው አማሮች ይኖራሉ፡፡ በ2010 መስከረም ወር ላይ እን ኦቦ ለማ መገርሳ እንዳሉት በኦሮሚያ ክልል ብቻ እስከ 11, 000, 000 የሚደርሱ ዐማሮች ይገኛሉ፡፡ በሌሎች አካባቢዎችም ከዚህ የሚበልጥ ቁጥር ያለው ዐማራ አለ፡፡ ይሁን እንጂ በመንግሥት ደረጃ በታቀደና በታሰበበት መንገድ የዐማራውን ቁጥር የማሳነስ ሥራ ሲሠራ ኖሯል፡፡ ብዛቱ ከሐገሪቱ ሕዝብ እስከ 50% የሚሆነውን የመሚሸፍን ሆኖ እያለ በቁጥር ሁለተኛ እንደሆነ ፐሮፓጋንዳ መነዛቱ፣ በሕዝብና ቤት ቆጠራ ሪፖርትም የሕዝብ ቁጥሩ እየቀነሰ መሆኑ፣
8.  በተለያዩ የሐገሪቷ አካባቢዎች በሥፋት ተሠራጭቶ የሚኖረው ዐማራ ዐማራ ነኝ ሲል ከመንግሥት ሊያገኝ የሚገባውን ጥቅም የሚያስከለክለው በመሆኑ ምክንያት፣ ልጆቹ ቢማሩም ባይማሩም የሥራ እድል እናዳያገኙ የሚገደዱ በመሆናቸውም ምክንያት ዐማራነታቸውን ትተው በሌላ ብሔረሰብ ስም እየተመዘገቡ እንዲኖሩ እየተደረገ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡
በመሆኑም እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩ ምክንያቶች ዐማራው የሐገር አልባነት ስሜት እንዲሰማውና ተረጋግቶ ሕይወትን መምራት እንዳይችል የሚያደርጉ፤ በሕይወቱም ተስፈኛ እንዳይሆንና በሐገሩ እየተሳቀቀ እንዲኖር የሚያደርጉ ናቸው፡፡ ከዚህም በላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ የቁጥር መቀነስን እያመጡ የአናሳ ናችሁ እኛ ከናንተ የበለጠ ጥቅም ማግኘት ይገባናል የሚሉ ትረክቶች እንዲያቆጠቁጡ እያደረገ ነው፡፡ የሕልውና አደጋ (ፈተና) ሲባልም ሙሉ ለሙሉ የመውደም ጉዳይ ሳይሆን የነበረን መሠረት የማሳጣት፣ የማኅበረሰብን ሥነ ልቡና የማዳከምና በሐገሩ ጉዳይ አንገቱን ደፍቶ ሁሌም ተበዝባዥ አድርጎ የማስቀጠል ጉዳይን የሚመለከት ነው፡፡


Wednesday, October 3, 2018

ሁሉንም በግል መነጽራችን ማየት የአብሮነት ጉዟችን ፈተና



ያለፉት ዐርባ አምስት (45) ዓመታት የኢትዮጵያ ፖለቲካ በመጠላለፍና ጣት መቀሳሰር የተሞላ እንደነበርና እንደሆነ የሚያሳዩን በርካታ ማስረጃዎች አሉ፡፡ ይህም በዛሬው ትውልድ ላይ የቀረውን ጠባሳ ሰፊ እንዲሆንና ዐዲስና የለውጥ መሠረት የሚባለው ወጣት ሃይል በከንቱ እንዲቀር አድርጓል፣ ዛሬም እያደረገ ነው፡፡

በነዚህ ዓመታት እንደአሸን የፈሉት የፖለቲካ ድርጅቶች የፖለቲካቸውን መሠረት ያደረጉት በጨቋኝ ተጨቋኝ ትርክት ላይ በመሆኑና የነሱን የአሸዋ ላይ ውትወታ ተከትለው በነፋሱ አቅጣጫ በመመራት ታሪክ ጻፍን ያሉ ግለሰቦችም ንቅዘትን ለትውልድ የሚያስተላልፉ ትርጉም አልባና የቁርሾና የቂም ጎተራ የሆኑ ጥራዞችን አምርተዋል፡፡ በተለይ ደግሞ ከሁሉም በከፋ መልኩ ይህንን የፖለቲካና የታሪክ ዕይታ በሰፊው እያቀነቀነ የነበረው ድርጅት የመንግሥትነትን ሚና ከተቀበለ በኋላ የነበሩት ለሠላሳ ፈሪ ዓመታት መነጣልና መጠራጠር በከፍተኛ ሁኔታ ያጎነቆለባቸውና አሽቶም የጎመራባቸው ጊዜያት ናቸው፡፡

ሁሉም የኔ የሚለው ጎሣ ሥር ለመጠለልና ምክንያትና ተጠየቅን ጉድጓድ ምሶ ለመቅበር ሲንደፋደፍ ራሱንና መሠረታዊ ማንነቱ ሰብአዊነትን አጉብጧል፡፡ ሁሉም ነገሮች የሚመዘኑበት መንገድም ከምክንያትና ከተጠየቅ ይልቅ ከጎሣ እና ከቋንቋ ወገንተኝነት በማስተሳሰር ሆኗል፡፡ አንደአንድ ሐገር ዜጎች ከምናስብ ይልቅ እንደበርካታ ትንንሽ ሐገሮች በምንቆጥራቸው ጎሣዎቻችን ጥላ ሥር እንድንወሸቅ ሆነናል፡፡

የራሰችንን ዜጋ ሐገርህ አይደለም በማለት ማፈናቀል ከጀመርን በርከት ያሉ ዓመታት የተቆጠሩ ቢሆንም ያለፈው 2010 ዓ.ም እና የጀመርነው 2011 ዓ.ም ግን እጅግ የከፋው (ክፋቱ ከሚፈጸሙት አሰቃቂ ግድያዎች አንጻር ብቻ ሳይሆን ከነካቸው ጎሣዎች እና ከተፈናቀሉት ዜጎች ቁጥርም ጭምር ነው) ይመስለኛል፡፡ ይህንነ መፈናቀል የበለጠ የከፋ የሚያደርገው ደግሞ ከመፈናቀል በኋላ የሚደረጉ የድጋፍ እንቅስቃሴዎች እየታዩ ያለበት ዕይታና የሚሰጣቸው የፖለቲካ ወገንተኝነት ትርጉምም ነው፡፡

ሐገሩ ወደዚህ ምስቅልቅል እንዴት ገባች ብሎ ከሚጠይቀው ይልቅ ማን ለየትኛው ተፈናቃይ ድጋፍ አደረገ የሚለውን ጉዳይ እያሳደደ ድጋፍ አድራጊውን አካል በጎሣና የፖለቲካ ወገንተኝነት ከረጢት ውስጥ ለመክተት የሚሽቀዳደመው ወጣት ቁጥር በብዙ እጥፍ ይልቃል፡፡ አንድ ዓመት በማይሞላ ጊዜ ውስጥ ከ2,000,000 የሚበልጥ ቁጥር ያላቸው የሐገሩ ዜጎች ከኖሩበት ቀየ መፈናቀላቸውና መጎሳቆላቸው ከሚያሳዝነው ይልቅ የትኛው ዝነኛ ሰው ኬት አካባቢ ለተፈናቀሉ ሰዎች ድጋፍ አደረገ? የትኛው አክቲቪስት ከየትኛው አካባቢ የተፈናቀሉ ሰዎችን ጉዳይ አራገበ? የመሳሰሉ ጥያቄዎችን እያነሳ ሲያራግብና አቧራ ሲያጨስ የሚውለው ወጣት ቁጥር የትየለሌ ሆኗል፡፡

መፈናቀልን ማስቆም የሚቻልበትንና ተከባብሮና ተስማምቶ መኖር የሚቻልባቸው መንገዶችን ከሚፈልገው ኃይል ይልቅ እከሌ ከዚህ አካባቢ የተፈናቀሉ ሰዎችን የረዳው እንትን ለተባለው ብሔረሰብ ቀና አመለካከት ስለሌለው ነው፤ ከእንትን አካባቢ የተፈናቀሉት ሰዎች ድጋፍ ተዥጎድጉዶላቸው ከእንትን አካባቢ የተፈናቀሉትን ቀና ብሎ የሚያያቸው ጠፋ፤ ወዘተ የሚሉ ጉዳዮችን እያነሳ እየጣለ ጉንጭ አልፋ ሙግት ሲሟገት የሚውለው ይበልጣል፡፡

ከኔ ቤት ምን ክፍተት አለ? ከሌላውስ በኩል? መፍትሔውስ ምንድን ነው? የሚሉ መሠረታዊ ጥያቄዎችን እያነሳ ችግር የሚቀርፍ ሐሳብ ከመለዋወጥ ይልቅ ሁሉም ሰው እኔ ባየሁበት መንገድ ማየት ካልቻለ ጠላቴ ነው የሚል ፍረጃ ውስጥ ገብቶ ለመሸናነፍና ለመዋደቅ ደፋ ቀና ሲል የሚታይበት ሆኗል፡፡

ሆኖስ ግን፤ ሁሌም ሰው በተፈናቀለ ቁጥር እርዳታ በማሰባሰብ መፍትሔ ማምጣት ይቻላል ወይ? አንድ ጊዜ እርዳታ ያሰባሰበ ቡድን ወይም እርዳታ የለገሰ ግለሰብና ቡድንን በዚህ የነቀዘ የፖለቲካ ሥርዓት ምክንያት ሰዎች በተፈናቀሉ ቁጥር እርዳታ የመስጠት ግዴታ አለበት ወይ? እርዳታ ማድረግ ችግሩን መስቆም ይችላል ወይ? የፖለቲካ ሥርዓቱ በዚህ መንገድ ከቀጠለ የሚፈናቀለው ሰው ከማይፈናቀለው የሚበልጥበት ጊዜስ ሊመጣ አይችልም ወይ? ያለበት አካባቢ የሁል ጊዜ መኖሪያው እንደሆነ ተማምኖ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ዜጋስ ምን ይህል ነው?

በመጨረሻም ችግራችንን የበለጠ የሚያሰፉ ጉዳዮች ላይ እየተነታረክን የሚያቃቅሩን እና የበለጠ አደጋው የሚያሰፉ ጉዳዮች ላይ ተጠምደን ከምንውል መፍትሐየ ሊያመጡልን በሚችሉ ጉዳዮች ዙሪያ ሐሳብ እየተለዋወጥን የአብሮነት መንገዳችንን ብንጠርግ የተሸለ ይሆናል ብየ አስባለሁ፡፡

Thursday, June 22, 2017

ጎጃም ኑራ ማሬ (ክፍል 1)

(የዘፈኑ ‹ሙዚቃው› አጠቃላይ ሁኔታ)
የት ነበር ያኖርኩት ቀፎዬን ስል ኖሬ
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኑራ ማሬ፡፡
ብራናየ አንች የልጅነት ጓዴ
ተረሳሽ ወይ የሳቱ ዳር ተረት ባንዴ::

በዘብህ የተሰደደው ፍቅሩን (ሰብለወንጌል መሸሻን) ጎጃም አስቀምጦ ነው፡፡ ጎጃም ተስፋው አለች፡፡ ተስፋው ተከትላው መምጣት አልቻለችም፡፡ ትመጣለች ብሎ እየጠበቃት የውኃ ሽታ ሆና ስትቀርበት ፍቆት ሽታውን ሊፈልጋት ተመልሶ ወደ ጎጃም ጉዞ ጀመረ፡፡ የጎጃምን ምድር ዳርቻውን እንደረገጠ በሽፍቶች ተደብድቦ መራመድ እንኳን አቅቶት መንገድ ላይ ወድቆ አንዲት ሴት ታገኘውና ታስጠጋዋለች፡፡ በተጠጋበት ቤት ተስፋው ተቆራምዳ፣ መንኩሳ ቢጫ ልብስ ለብሳ ያገኛታል፡፡ በጣዕርና በሳቅ መሐል ሆኖ ሕይወቱ ታልፋለች፡፡

ይህ ፍቅር እስከመቃብር የተሰኘው ድንቅ መጽሐፍ የሚተርክልን ጉዳይ ነው፡፡ ይሀንን ነገር ቴዎድሮስ ካሳሁን በሙዚቃ ሰርቶ ሲያመጣልን ፍቅር እስከመቃብር የያዘው አድማስ ብቻ እንዲበቃው ሆኖ የቀረበ ሆኖ አይታየኝም፡፡ ይህንን እምነቴን ያስረዱልኝ ዘንድ ሁለት ነገሮችን እጠቅሳለሁ (ለጊዜው)፡፡

1.     1.  ዜማው፡- ሲጀምር ከቅዳሴ ዜማ ይነሳና ወደሚያስደልቅ ደማቅ የጎጃም ባሕላዊ ጭፈራ ምት ይሸጋገራል፡፡ ቅዳሴ በጎጃም ማኅበረሰብ ትልቅ ሥፍራ የሚሰጠው ከገበሬው እስከ ካህናቱ ቅዳሴ ቢታጎል መዓት የሚወርድባቸው፤ አምላካቸው ወደ ምድር መጥቶ ተሰቃይቶ የሚሞት የሚመስላቸው ናቸው፡፡ ቅዳሴ ከተጀመረ በኋላ ማንም እንዳይገባ የደጀ ሰላማቸውን በር ግጥም አድርገው ዘግተው በጥሞና የሚከታተሉ፣ በሩ ተከፍቶ ሰው ጥሶ ከገባ አካላቸው የተረገጠ ያህል ስቅቅ የሚላቸው፣ መላእክት ወደምድር መጥተው ለአምላካቸው እየሰገዱና እያሸበሸቡ እያለ ተረገጡ ብለው የሚያምኑ ናቸው፡፡ ሥለሆነም ዜማው በቅዳሴ መጀመሩ ስራው ማኅበረሰቡን በጥልቀት ከማየትና ከመረዳት የመነጨ መሆኑንና እጅግም በጥንቃቄ የተሠራ መሆኑን ያሳያል፡፡

ዜማው በቅዳሴ እንጀመረ በዚያው አይቀጥልም፡፡ አንጀት ወደሚበላ ነገር ግን ወደለቅሶ በሚመራ ደማቅ ዜማ ይሸጋገራል፡፡ ጎጃሞች የሚደልቁት ሲደሰቱ ብቻ አይደለም፤ ሲያዝኑም አንጂ፡፡ ጎጃሞች ሰው ሲሞት በየአድባሮቻቸው አደባባይ በመገኘት ሙሾ ያወርዳሉ፡፡ ሙሾው እጅግ ግጥም አዋቂነታቸው በተመሰከረላቸው  አስለቃሾች እየተመራ በረገዶ ታጅቦ በእናቶች ደረት ድቂ እየደመቀ የተለየ የሐዘን ስሜትን የሚፈጥር ዜማ ይፈጥራል፡፡ ዜማው እንጉርጉሮም ድለቃ የሚመስል ድምፀትም ያለው ነው፡፡ ይህ ድምፀት ነው በቴዎድሮስ ካሳሁን “ማር እስከ ጧፍ” ሙዚቃ ውስጥ የሚስተዋለው፡፡

ጎጃሞች በደስታቸው ወቅት መንደራቸው ምድርን በሚያንቀጠቅጥ ድለቃ ይቀልጣል፡፡ አዝመራ ከመሰብሰብ እስከሌሎች ማኅበራዊ ሁነቶች ባለው የእርስበርስ ግንኙነታቸው የደመቀ ጭፈራ ከመንደሮቻቸው አይጠፋም፡፡ ጧፍ ውስጥ የሚገኙት ቁጢቶች ሰም አስተባብሮ እንዳያያዛቸው ጎጃሞችን አጣምሮ የሚያያይዛቸውና ኑሯቸውን በሕብረት እንዲመሩ የሚያደርጋቸው ፍቅር ነው፡፡ ያ ፍቅራቸው ደግሞ የሚገለጸው ልብን በሚያሞቀው ዜማቸው ነው፡፡ ዜማ የሁሉ ነገራቸው መግለጫ መሣሪያ ነው፡፡ ዓይነቱ ይለያይ ይሆናል እንጂ፡፡

22. በግጥሙ ውስጥ የሚጠቀሱት ቃላት፡- በዚህ ሙዚቃ ግጥም ውስጥ ቴዎድሮስ ካሳሁን የተጠቀማቸው ቃላት እጅጉን ለጎጃምና ጎጃሜዎች የቀረቡ ናቸው፡፡ ይህም ከያኒው ሥራውን ለመሥራት ምን ይህል ስለማኅበረሰቡና ማኅበረሰቡ ላይ ትኩረቱን አድርጎ ስለተጻፈው ፍቅር እስከመቃብር መጽሐፍ በጽሞና አንዳሰላሰለ የሚያሳይ ነው፡፡ “የፀበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል” ይላል የዘፈኑ ግጥም ጀመሪያ ስንኝ፡፡ ፀበልና እንኮይ ከጎጃም ማኅበረሰብና ልጆች ጋር ከፍተኛ ትስስር ያላቸው ናቸው፡፡ ፀበል በጎጃም ማኅበረሰብ ዘንድ እጅግ የተከበረና ከማንኛውም ዓይነት የሕክምና ተግባር ቅድሚያ የሚሰጠው ፈውስ የማግኛ መንገድ ነው፡፡ እናም ከያኒው ሰብለወንጌልን ለመግለጽ የተጠቀመው፡፡

ኑራ-በተለመደው ዐማርኛ የሆነ ቦታ (ሥፍራ) ቆይታ የሚል ፍቺ አለው፡፡  ሌላ ተጨማሪ ፍቺም ይሸከማል፡፡ አንድም የሆነ ቦታ እያለች (ሳለች) ነው ለካ… የሚል፤ አንድም ለካ እሷ ናት እንደማለት፡፡ በቴዲ አፍሮ ዘፈን ተደጋግሞ የሚጠራው ቃልም “ጎጃም ኑራ ማሬ” የሚል ነው፡፡ ጎጃም “ጎጃም ኑራ ማሬ” ሲል አንድም በዛብህን የወከለው ሰው ሰብለ ወንጌልን ሸዋ ሲጠብቃት እሷ ግን ጎጃም ያች መሆኗን አመልካች ነው፡፡ አሊያም የኔ መድኃኒት ጎጃም ነች እንደማለትም አድርገን መውሰድ እንችላለን፡፡

ማር ከጣፋጭነቱ በተጨማሪ መድኃኒትነቱ ፍቱን የሆነ መሆኑ የታወቀ ሐቅ ነው፡፡ (ይቀጥላል-- ተጠናክሮ)


 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡