ከፀሐይ በስተጀርባ
ፀሐይ እየወጣች ነው፡፡ የተደበቀው ጉድፍ ሁሉ በአደባባይ ይገለጣል፡፡ በየጥሻው የተወሸቀው ሁሉ ለሕዝብ ይታያል፡፡ ድምጽን
አጥፍቶ የተሠራው ሁሉ በከፍተኛ ድምጽ ይጮሃል፡፡ ረግቶ የነበረው ሁሉ በከፍተኛ ፍጥነት ይንቀሳቀሳል፡፡ አንቀላፍቶ የነበረው ከተማ
በድንገተኛ ትርምስ ይታጀባል፡፡ አቀርቅሮ የነበረው በረንዳ ሁሉ አንገቱን ቀና ያደርጋል፡፡
ገና በማለዳው ቢራ
እየጠጣሁ ነው፡፡ የሚያየኝ ሁሉ ‹‹በሰላም ነው እንዴ?›› እያለ ይጠይቀኛል፡፡ እኔ ለዓመታት ያደረግኩት ስለሆነ ምንም አይሰማኝም፡፡
ዛሬ ግን ከሰፈሬ ርቄ ነው የምጠጣው፡፡ ስድስት ኪሎን ለቅቄ ጎፋ ካምፕ ሔጃለሁ፡፡ እዚያ ማንም አያውቀኝም፤ ለምን ብሎ የሚጠይቀኝም
የለም፡፡ ማንኛውንም ነገር እንደፈለግኩ መፈጸም እችላለሁ፡፡
ሦስት ቢራ አጠናቅቄ
አራተኛውን አጋምሸዋለሁ፡፡ ሞቅታ እየተሰማኝ እንደሆነ ፊቴ ላይ ችፍ ባለው ላቭ ማወቅ ይቻላል፡፡ በምኖርበት ሰፈር ጨለማን ጠብቄ
የማደርገውን ዛሬ በብርሃን ለፈጸም ወሰንኩ፡፡ ሁለት ሴቶች በአንድ ላይ የተቀመጡ መሆናቸውን አየሁ፡፡ ያለምንም ማመንታት ተነስቼ
ወደነሱ ሔድኩ፡፡ ያለምንም ጥያቄ ተቀላቀልኳቸው፡፡ ፊታቸው ላይ የመደንገጥ ስሜት ባይታይም ለመቆጣት ሞከሩ፡፡ ‹‹ከደበራችሁ መነሳት
እችላለሁ›› አልኳቸው፡፡ ‹‹በል አርፈህ ተቀመጥ›› አለችኝ ጠቆርና ቀጠን ያለችው ልጅ፡፡
እድሜያቸው ከአሥራ
ስምንት ዓመት አያልፍም፡፡ ገና ሲታዩ የሚያሳሳ ውበት ተሸክመዋል፡፡ ተመሳሳይ ቀለም ያለው ለብሰው አንድ ዓይነት ቦርሳ ይዘዋል፡፡ ከቆዳ ቀለማቸው በስተቀር በማንኛውም
ነገር ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ከአነጋገር እስከ አረማመዳቸው አንዷ የአንዷ ቅጅዎች ናቸው፡፡ እንዳየኋቸው መንትያዎች መሆናቸውን ነው
የገመትኩት፡፡ እናም የመጀመሪያ ጥያቄየ የሆነው ‹‹መንትዮች ናችሁ እንዴ?›› የሚለው ነበር፡፡
‹‹ሃ!ሃ! አነወመስልም?››
መለሰች ቀላ ብላ ወፈር ያለችው ሴት፡፡ ‹‹ስለመሰላችሁኝማ ነው የጠይቅኳችሁ›› አልኳት፡፡ ‹‹እሱን ቆይተን እንደርስበታለን፡፡
ይልቅ አሁን ምን ትጋብዘናለክ?›› አለችኝ፡፡
‹‹የሚጠጣ ነው?››
‹‹ሆ! ሆ! ኧረ ገና
ቁርስ አልበላንም፡፡ የሚበላ ነገር፡፡ …›› አለች፡፡
‹‹እናንተ የመረጣችሁት
ይሁና! መቸም እናንተን የመሰሉ የቆንጆ መለኪያዎች ጋር ተቀምጦ አልጋብዝም ማለት ውርደት ነው፡፡›› አልኳቸው፡፡ እንደ ድሮው ቢሆን
ኖሮ እንኳን እነሱን የምጋብዝበት የራሴን ቢራ የምጎነጭበት ሰባራ ሳንቲም እንኳን ሊኖረኝ አይችልም- ለዛውም በዛሬዋ ዕለት- የወሩ
መጨረሻ በቀረበባት በሃያ ሁለተኛዋ ቀን፡፡ እድሜ ለዚያ መላጣ ፈረንጅ፡፡ በሽዎች የሚቆጠሩ ዶላሮችን ዘርግፎልኝ ሔዷል፡፡
ጠቆር ያለችው ሴት
አጨበጨበች፡፡ አስተናጋጁ የኋላ እግሩ እንደ ተሰበረ በሬ ሳብ ጉብ እያለ መጣ፡፡ ‹‹ምን ልታዘዝ?›› በሰለለ ድምጽ ጠየቀ፡፡ ‹‹የቤቱን ስፔሻል፡፡ … ደግሞ በጥሩ ሁኔታ ይሠራልን እሽ!››
ብላ በመብረቅ ዐይኗ ጠቅ አደረገችው፡፡ በደስታ ሰክሮ ‹‹ጥይት እንደሳተው›› እየተደናበረ ሔደ፡፡
‹‹ተጫዎት!›› አለች
ቀይነት ያላት፡፡
‹‹እየተጫዎትኩ ነው››
መለስኩ፡፡
‹‹ለደቂቃዎች አብረን ተቀመጥን፤ ነገር ግን እስካሁን አልተዋወቅንም፡፡ እሷ
ኤልሲ እኔ ደግሞ ሳሪ እንባላለን፡፡ አንተስ ማን ትባላለህ?››
‹‹እ! የኔ ስም እንኳን
ቢቀር ይሻላል፡፡ በጣም ረዥም እና ለመያዝም የሚያስቸግር ነው፡፡››
‹‹ማለት?››
‹‹የኔ ስም ከሦስት
መስመር ያልፋል፡፡ ዓለም ከኔ በፊት አይታው የማታውቅ ድንቅና ብርቅየ ስም ነው፡፡››
‹‹እውነት! እስኪ
ንገረንና እንስማዋ!››
(ይቀጥላል….)
No comments:
Post a Comment