ገና ከጅምሩ፣
አንቺ ስትመሪ ስከተልሽ ኖሬ፣
ፍቅር በተባለ ገመድሽ ታስሬ፣
ያመጣኝን መንገድ ዛሬ ሳየው ዞሬ፣
ወከክ ብየ ቀረሁ አንገቴን ሰብሬ፤
መቼስ ለምን ካልሽኝ፡-
አንቺ አንቺን እያለ ተከትሎሽ እግሬ በመንደፋደፉ፣
ተስቦ ተገፍቶ አቀበቱን ወጥቶ ሲደርስ ከአፋፉ፣
በግልምጫሽ ብቻ ልቤ ሲደነግጥ ግፍፍ ሲል ቀልቡ፣
ወኔ እና ተስፋዬ በነፋስ ሽውታ ተንነው ገደል ገቡ፤
እናም፣
መውደድ እና ፍቅር ብርታት እየሰጡ እያሉኝ በል ግፋ፣
የወጣሁት ዳገት ወኔን ተመርኩዤ ታጅቤ በተስፋ፣
መልሶ ለመውረድ ጭንቅ ጥብ ሆኖብኝ የበረታ ዳፋ፣
ቁልቁል ተንደርድሬ ባናቴ እንዳልል ትክል ሔጄ እንዳልደፋ፣
ከተነሳሁበት መልሶ የሚያደርስ መሹለኪያ የሚሆን ከማጥ የሚያወጣ፣
መንገድ ምሪኝ እና ጭንቄን ልገላገል ካስገባሽኝ ዓለም ከሰመመን
ልውጣ፡፡