Saturday, June 20, 2020

ዛሬ እንዴት አነሰ?

ትላንት ያወደስነው ስሙን የጠራነው አክብረን በደስታ፣

ዜማ ያዜምንለት ጀግና ነህ እያልነው መጽናኛ መከታ፣

“አብሪ ኮከብ ሆኖ እየተተኮሰ፣

የነጻነት ችቦን ቀድሞ የለኮሰ፣

አጽናፍን አዳርሶ ሥሙ የነገሠ፣

ኩስምን ሁነቶችን ግርማ እያለበሰ፣

ገንኖ እያገነነ ዐለምን መዳፏን አፏ ላይ ያስጫነ፣

ከተናቁት መሀል አስናቂ እንዲወጣ ሠርቶ ያሳመነ፣”

እያልን የካብነውን ከፍ እያደረግን አውጥተን ከማማ፣

ገድየ አሞታለሁ ያልንለት በክፉ ሲነሳ ሲታማ ስንሰማ፤

 

ዛሬ፡-

ካለፈ በኋላ ጉድጓድ ውስጥ ከገባ አፈር ከለበሰ፣

አጥንቱ ከላመ፤ ሥጋው አፈር ሆኖ ገላው ከፈረሰ፣

ዐለም ከረሳችው ከውጣ-ውረዷ ከተሰናበተ፣

በሌለበት ጊዜ፣ መልስ በማይሰጠን እየተሟገተ፣

ከየጥጋጥጉ ጥያቄዎች በዙ የክስ ጎርፍ ጎረፈ፣

አርነት ያወጣ መንገድ እያበጀ ጠርጎ ያሳለፈ፣

እያልን ያወራነው ያ ሁሉ ውዳሴ ያ ሁሉ ሙገሳ፣

ሰውየው ቢጠፋ ከምኔው ተተወ ከምኔው ተረሳ?

ስሙን ያጠቆርነው ጥላሸት የዋጣው ማቅን የለበሰ፣

ከትላንቱ ግብሩ አሁን ምኑ ታጣ? ዛሬ እንዴት አነሰ?


No comments:

 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡