Monday, June 22, 2020

እርም ለበላ ትግል ...

ምላስህ ላይ ቆሞ ሲጮህ እየዋላ፣

ትከሻህ ለይ ኾኖ በአንተው እየማለ፣
ስላንተ ሊታገል ድርጅት ፈልፍሎ እንዳሸን የፈላ፣
ብዙ ወገን አለህ ከጉሮሮህ ነጥቆ ሆዱን የሚሞላ፣
በደል ተጠይፎ ጉስቁልናህ ከብዶት፣
በመከራህ አዝኖ ያንተ ሕመም አሞት፣
አማራጭ የሚሆን ሊቀድ ዐዲስ ፈሰስ፣
ጥቃትህን ሊመክት እንባህንም ሊያብስ፣
እያሽሞነሞነ በቃላት ከሽኖ ዲስኩሩን በጆሮህ እያንቆረቆረ፣
ያንተ ወኪል ሆኖ ሲፋጭ እንደሚውል ስላንተ እያረረ፣
አደባባይ ቆሞ ሲሰብክ የሚውለው ተሳደድኩ እያለ የሚብከነከነው፣
የአንተ ማጣት መንጣት እየቆረቆረው ሰቅዞ እየያዘው እረፍት እየነሳው፣
መሆኑን ሲነግርህ ደጋግመህ ስትሰማ፣
የትግሉን መሠረት ዕቅድ እና ዓላማ፣
እምነት ጥለህበት የተነሳህለት ያቆመህ ከጎኑ፣
የምትሰዋለት እሱ በጀመረው በያዘው ውጥኑ፣

ዳግመኛም፡-
ችግርህ ተቀርፎ ትንን ብሎ ጠፍቶ አልፎ ሰቀቀኑ፣
ፋና እንዲበራልህ ጨለማህ ተገፍፎ እንዲነጋ ቀኑ፣
"ከእሱ በፊት እኔ፤ እንዲነጋ ቀኔ፣
ወገቤ እየጠና እንዲደረጅ ጎኔ፣
ግፉ እንዲያበቃልኝ የያዘኝ ኩነኔ፣
ባደግሁበት ምድር መኖር በምናኔ፣
እሱ ይከተለኝ እቀድማለሁ እኔ፣"
ያልህለት ታጋይህ ከመንገዱ ወጥቶ፣
ቆምሁለት ያለውን ዓላማውን ትቶ፣
በስምህ ነግዶ ትርፉን አደርጅቶ፣
ከፍ ከፍ እያለ ዝናው ተንሰራፍቶ፣
ዞሮ የማያይህ ሆኖ ስታገኘው ውለታን የረሳ፣
ትናንቱን ዘንግቶ እንዴትና ለምን የት እንደተነሳ፣
ቅስምህን ቢሰብረው አንጀትህ ቢከስል ቢገኝ ተኮማትሮ፣
አንተው ለራስህ ቁም እሱ ሆዱን እንጂ አያይህም ዞሮ፤

እንጂማ!
ቆሞልኛል ብለህ የምትከተለው፣ ያድነኛል ያለኸው፣
በስምህ የማለው በአንተ የሚገዘተው፣
ጥምህ የሚሰማው መራብህን የሚያየው፣
እርዛትህን ቀርፆ ምስሉን የሚይዘው፣
መሰላሉ ሆኖት እያሸጋገረው ከዙፋን ላይ ወጥቶ፣
አንተኑ ሊበላህ ቀድሞ የጋጠህን እንዳዲስ ተክቶ፣
አመዳይ ሊያለብስህ የእግሩ መርገጫ አርጎ፣
ገትኖ ሊበላህ በአንተው ወዝ አምጎ፣
ካልሆነ በስተቀር፣
እጥፍ ብሎ አንጀትህ መንምነህ እያየህ ሰውነትህ ጫጭቶ፣
ሙግግ ክስት ብለህ የለበስኸው ቆዳህ እላይህ ላይ ለፍቶ፣
ችጋር አንቆ ይዞህ ሆድህ ተሰልቅቦ ከጀርባህ ተጣብቆ፣
ማጣትህ መንጣትህ አደባባይ ወጥቶ ሲውል ፀሐይ ሙቆ፣
ሙቶ ከከረመ አጽሙ አፈር ከሆነ፣
ከዓለም ተሰናብቶ ምእት ከደፈነ፣
ሲሟገት አይውልም አስክሬን ቀስቅሶ፤
አልያም
ግዑዝ ከሆነ አካል ጆሮው ከማይሰማ ከድንጋይ ምሰሶ፣
ሲታከክ አይውልም በድንጋይ ላይ ቆሞ ድንጋይ ተንተርሶ፤
ስለዚህ ወንድም ሆይ!

እሱን ተወውና ልቡናህን አድስ፤ ራስህን አንጽ በራስህ ላይ ሥራ፣
ባንተ ላይ ተራምዶ ወደ ላይ ከወጣ ጆሮውም አይሰማ ደጋግሞ ቢጠራ፡፡

No comments:

 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡