Monday, June 22, 2020

እርም ለበላ ትግል ...

ምላስህ ላይ ቆሞ ሲጮህ እየዋላ፣

ትከሻህ ለይ ኾኖ በአንተው እየማለ፣
ስላንተ ሊታገል ድርጅት ፈልፍሎ እንዳሸን የፈላ፣
ብዙ ወገን አለህ ከጉሮሮህ ነጥቆ ሆዱን የሚሞላ፣
በደል ተጠይፎ ጉስቁልናህ ከብዶት፣
በመከራህ አዝኖ ያንተ ሕመም አሞት፣
አማራጭ የሚሆን ሊቀድ ዐዲስ ፈሰስ፣
ጥቃትህን ሊመክት እንባህንም ሊያብስ፣
እያሽሞነሞነ በቃላት ከሽኖ ዲስኩሩን በጆሮህ እያንቆረቆረ፣
ያንተ ወኪል ሆኖ ሲፋጭ እንደሚውል ስላንተ እያረረ፣
አደባባይ ቆሞ ሲሰብክ የሚውለው ተሳደድኩ እያለ የሚብከነከነው፣
የአንተ ማጣት መንጣት እየቆረቆረው ሰቅዞ እየያዘው እረፍት እየነሳው፣
መሆኑን ሲነግርህ ደጋግመህ ስትሰማ፣
የትግሉን መሠረት ዕቅድ እና ዓላማ፣
እምነት ጥለህበት የተነሳህለት ያቆመህ ከጎኑ፣
የምትሰዋለት እሱ በጀመረው በያዘው ውጥኑ፣

ዳግመኛም፡-
ችግርህ ተቀርፎ ትንን ብሎ ጠፍቶ አልፎ ሰቀቀኑ፣
ፋና እንዲበራልህ ጨለማህ ተገፍፎ እንዲነጋ ቀኑ፣
"ከእሱ በፊት እኔ፤ እንዲነጋ ቀኔ፣
ወገቤ እየጠና እንዲደረጅ ጎኔ፣
ግፉ እንዲያበቃልኝ የያዘኝ ኩነኔ፣
ባደግሁበት ምድር መኖር በምናኔ፣
እሱ ይከተለኝ እቀድማለሁ እኔ፣"
ያልህለት ታጋይህ ከመንገዱ ወጥቶ፣
ቆምሁለት ያለውን ዓላማውን ትቶ፣
በስምህ ነግዶ ትርፉን አደርጅቶ፣
ከፍ ከፍ እያለ ዝናው ተንሰራፍቶ፣
ዞሮ የማያይህ ሆኖ ስታገኘው ውለታን የረሳ፣
ትናንቱን ዘንግቶ እንዴትና ለምን የት እንደተነሳ፣
ቅስምህን ቢሰብረው አንጀትህ ቢከስል ቢገኝ ተኮማትሮ፣
አንተው ለራስህ ቁም እሱ ሆዱን እንጂ አያይህም ዞሮ፤

እንጂማ!
ቆሞልኛል ብለህ የምትከተለው፣ ያድነኛል ያለኸው፣
በስምህ የማለው በአንተ የሚገዘተው፣
ጥምህ የሚሰማው መራብህን የሚያየው፣
እርዛትህን ቀርፆ ምስሉን የሚይዘው፣
መሰላሉ ሆኖት እያሸጋገረው ከዙፋን ላይ ወጥቶ፣
አንተኑ ሊበላህ ቀድሞ የጋጠህን እንዳዲስ ተክቶ፣
አመዳይ ሊያለብስህ የእግሩ መርገጫ አርጎ፣
ገትኖ ሊበላህ በአንተው ወዝ አምጎ፣
ካልሆነ በስተቀር፣
እጥፍ ብሎ አንጀትህ መንምነህ እያየህ ሰውነትህ ጫጭቶ፣
ሙግግ ክስት ብለህ የለበስኸው ቆዳህ እላይህ ላይ ለፍቶ፣
ችጋር አንቆ ይዞህ ሆድህ ተሰልቅቦ ከጀርባህ ተጣብቆ፣
ማጣትህ መንጣትህ አደባባይ ወጥቶ ሲውል ፀሐይ ሙቆ፣
ሙቶ ከከረመ አጽሙ አፈር ከሆነ፣
ከዓለም ተሰናብቶ ምእት ከደፈነ፣
ሲሟገት አይውልም አስክሬን ቀስቅሶ፤
አልያም
ግዑዝ ከሆነ አካል ጆሮው ከማይሰማ ከድንጋይ ምሰሶ፣
ሲታከክ አይውልም በድንጋይ ላይ ቆሞ ድንጋይ ተንተርሶ፤
ስለዚህ ወንድም ሆይ!

እሱን ተወውና ልቡናህን አድስ፤ ራስህን አንጽ በራስህ ላይ ሥራ፣
ባንተ ላይ ተራምዶ ወደ ላይ ከወጣ ጆሮውም አይሰማ ደጋግሞ ቢጠራ፡፡

Saturday, June 20, 2020

ዛሬ እንዴት አነሰ?

ትላንት ያወደስነው ስሙን የጠራነው አክብረን በደስታ፣

ዜማ ያዜምንለት ጀግና ነህ እያልነው መጽናኛ መከታ፣

“አብሪ ኮከብ ሆኖ እየተተኮሰ፣

የነጻነት ችቦን ቀድሞ የለኮሰ፣

አጽናፍን አዳርሶ ሥሙ የነገሠ፣

ኩስምን ሁነቶችን ግርማ እያለበሰ፣

ገንኖ እያገነነ ዐለምን መዳፏን አፏ ላይ ያስጫነ፣

ከተናቁት መሀል አስናቂ እንዲወጣ ሠርቶ ያሳመነ፣”

እያልን የካብነውን ከፍ እያደረግን አውጥተን ከማማ፣

ገድየ አሞታለሁ ያልንለት በክፉ ሲነሳ ሲታማ ስንሰማ፤

 

ዛሬ፡-

ካለፈ በኋላ ጉድጓድ ውስጥ ከገባ አፈር ከለበሰ፣

አጥንቱ ከላመ፤ ሥጋው አፈር ሆኖ ገላው ከፈረሰ፣

ዐለም ከረሳችው ከውጣ-ውረዷ ከተሰናበተ፣

በሌለበት ጊዜ፣ መልስ በማይሰጠን እየተሟገተ፣

ከየጥጋጥጉ ጥያቄዎች በዙ የክስ ጎርፍ ጎረፈ፣

አርነት ያወጣ መንገድ እያበጀ ጠርጎ ያሳለፈ፣

እያልን ያወራነው ያ ሁሉ ውዳሴ ያ ሁሉ ሙገሳ፣

ሰውየው ቢጠፋ ከምኔው ተተወ ከምኔው ተረሳ?

ስሙን ያጠቆርነው ጥላሸት የዋጣው ማቅን የለበሰ፣

ከትላንቱ ግብሩ አሁን ምኑ ታጣ? ዛሬ እንዴት አነሰ?


Sunday, June 7, 2020

እንደግመል ሽንት ሁልጊዜም የኋሊት፤ አይሰለችም?

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን የጉዞውን መነሻ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ብቅ ባሉት ጋዜጣዎች ጀምሮ በዓይነት እና በቁጥር እየሰፋ ዛሬ ላይ ያለበት ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ጋዜጣ ምዕት ዓመት የሞላው ሲሆን የመጀመሪያው ሬዲዮ ጥር 23፣ 1927 ዓ.ም. ሥርጭቱን ከጀመረ 85 ዓመታትን አልፏል፤ የመጀመሪያው የቴሌቪዥን ጣሚያም ሥርጭቱን በ1957 ዓ.ም ከጀመረ 55 ዓመታትን ተጉዟል፡፡ ይህም የኢትዮጵያ ሚዲያ ዛሬ ላይ የተሳካላቸው እና ተጠቃሽ ሚዲያዎች ካሏቸው በርካታ ሀገራት ቀድሞ የተጀመረ መሆኑን ያሳያል፡፡

ዕድሜው የመርዘሙን ያህል ግን ሚዲያው እና ጋዜጠኝነቱ እያደገ ከመምጣት ይልቅ ወደ መጣበት አዙሮ እያየ የኋሊት ጉዞን የመረጠ እንዲመስል አድርጎታል፡፡ በቅርብ ዓመታት በርከት ያሉ የሬዲዮ እና የቴሌቪዥን ጣቢያዎች እንዲሁም የሕትመት ሚዲያዎች ተመሥርተውና ፈቃድ ተሰጥቷቸው ሥራ ቢጀመሩም የሚዲያውን የቀደመ አካሔድ ከማስተካከል እና ጉብጠቱን ከማረቅ ይልቅ ከጉብጠቱ ጋር ተስማምተው መኖርን የመረጡ መሆናቸውን ማንም የሚዲያዎቹ ተካታታይ ይታዘባል፡፡ የመጀመሪያዎቹ ተቋማት የአንድ ወገን የፕሮፓጋንዳ መሳሪያዎች ሆነው መጡ፣ ዛሬም ቀጠሉበት፡፡ ለመረጃ ትክክለኝነት እና ለዘገባ ሐቀኝነት ከመጨነቅ ይልቅ እገሌ የተባለውን ባለሥልጣን እንዳላስከፋ በምን መንገድ ላቅረበው በሚል ጉዳይ የሚጨነቁ ናቸው፡፡ አዳዲሶቹም በዚሁ ገፉበት፡፡

ቁጥራቸው እየጨመረ ቢመጣም የሚዲያን ሚና እና የጋዜጠኝነት አሠራርን እያሳደጉ ከመጓዝ ይልቅ ወደኋላ የሚጎትት እና የሚያቀጭጭ አካሔድን መርጠው እየተንከላወሱ ነው፡፡ ከጊዜ ወደጊዜ ሥሕተታቸውን እያረሙና እየተሻሻሉ ከመሥራት ይልቅም በቡድን ተከፋፍለው የመቆራቆሻ መሣሪያ ሆነዋል፡፡ ይህም የሚዲያውን ዕድገት ወደትናንት ከመጎተቱም በላይ ሲጀመር ከነበረበት ደረጃው ዝቅ አድርጎ ወደመድፈቅ እያንደረደራቸው ነው፡፡

የፖለቲከኞች ቁርቁስ እየሰፋ ሲመጣ ሚዲያዎቹም - በተለይም ከሕዝብ ከሚሰበሰብ ግብር በሚመደብላቸው ገንዘብ የሚንቀሳቀሱት ሚዲያዎችም ለተቆራቋሾቹ ወግነው በመቆም በእሳት ላይ ቤንዚን እየጨመሩ ይገኛሉ፡፡ ይህንን የሚያደርጉበት መንገድም ከእስከዛሬው አመጣጣቸው ሁሉ እየከፋና እየወረደ መጥቷል፡፡ እስከዛሬ በነበራቸው ጉዞ እውነትን በመካድ የአንድ ወገን መረጃን ማቅረብ የነበረ ሲሆን ዛሬ ላይ ግን አንዱ የሚዲያ ተቋም የዘገበውን ቆራርጦ ያልተባለን ሐሳብ እንደተነገረ አድርጎ ማቅረብ ላይ ደርሷል፡፡ የመረጃ ሽቀባው ከእርስ በርስ መረጃዎቻቸው ዓልፎ የሌላ ሀገር ሚዲያ ዘገባን መሸቀብ ላይ ደርሷል፡፡ ይህም አንድ ወይም ሁለት የሚዲያ ተቋማት ብቻ የሚገለጹበትና እና የሚወነጀሉበት ጥፋት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉ የሚዲያ ተቋማት የአብዛኞቹ መገለጫ ነው፡

ይህ ሁሉ ሲታይ የኢትዮጵያ ሚዲያ እና የጋዜጠኝነት አሠራር ወደፊት ከመገሥገሥ ይልቅ ወደኋላ መንሠራተትን መሥፈርት አድርጎ የሚሠራ አስመስሎታል፡፡ በዚህ ሁኔታ ላይ እንዳሉ እና እንደሚሠሩ እየታየም በቁጥር መበርከታቸውን እና የሚፈልገውን ሐሳብ ሲያንጸርቁለት እያየ የኢትዮጵያ ሚዲያ እድገት እያሳየ እንደሆነ የሚገልጽ እና የሚሟገት ሰውም (“ምሁር”) ቁጥሩ በርከት ያለ ነው፡፡ ይህንንም እንደስኬት ወስደውት እንደድጥ በፍጥነት ወደኋላ እያንሸራተታቸው ነው፡፡

መቼ ይሆን ይህ አሠራራቸው የሚቀየረው? መቼ ይሆን ቁልቁለት ለመውረድ ከመንደርደር ይልቅ ቀበት ለመውጣት መዳህ የሚጀምሩት?


Friday, February 14, 2020

የተስፋ ሰንሰለት



የመሸ ቢመስልህ የገባ ብርሃን የወጣ ጨለማ፣
ተስፋህ ተመናምኖ ብርክ ቢሆን ጭንቀትህ ቢሰማ፣
ኑሮህ ቢያስጎነብስ የእንብርክክ ቢያስጊዝም ግስም እያረገፈ፣
ተረት ቢያስተርትህ “ተንጋለው ቢተፉ…” ቢያሰኝህ ይህስ ቀን ባለፈ፣
ከድጡ ለማምለት እያውተረተረ መልሶ እየጣለህ ቢከትህ ከማጡ፣
እጅ አትስጠው ለእሱ የማይቀር ነው እና ነገ መለወጡ፣
በአለበሰህ ጭቃ ለራሱም በተራው ገብቶ መላቆጡ፣
ሕጉ በመኾኑ የተፈጥሮ ዑደት፣ ቢዘገይም ለውጡ፣
ድል መንሳት አይቀርም በሕወት ጉዞ ላይ ተስፋ ካልቆረጡ፡፡

እናልህ ወንድሜ፣
በዛሬ ላይ ትናንት ጠል እንዳይጥልበት፣
ደይኖ እንዳይይዘው ተክቶት ነግሦበት፣
ነገን አጠንዝሎ አክስሎት እንዳያልፍ፣
በእውቀትህ ከመራኸው ዛሬ ሳይዛነፍ፣
በእናት ማባበያ ልጅን መደለያ በእነእሰጥሃለሁ ኋላ “ጉዳጉዶ”፣
ካልተደለለ ሆድ ሚዛንን አስቶ በጥቅም ለውጦ ኅሊናን አስክዶ፣
የማታ የማታ ማሸነፍ አይቀርም ማየት ጠላት ወድቆ፣
ከቁዘማህ መውጣት በመንሰቅሰቅ ፋንታ መገኘት ፈንድቆ፡፡

ስለዚህ ወንድም ሆይ፡-
ሳንካ የሆነብህ መንገድ እየዘጋ፣ ግድግዳው ይወድቃል ተንኮታኩቶ ደቅቆ፣
መንገድህ ይጠራል ያንተ ጥረት ውጤት ከብሮ ሊታይበት ሊቆምበት ደምቆ፣
ጨለማው ይሸሻል በወጋገን ጨረር ጎኑ እየተወጋ ዛል ጥንዝል ብሎ፣
ተስፋህ እሸት ኾኖ ጎመራል የበለጠ ደምቆ የነገን ድል አዝሎ፣
እናማ፣
ዛሩህን ከያዝኸው ተጠንቅቀህለት አክብረኸው ከኖርህ የሕይወትን ሥራ፣
ነገህ ይክስሃል ወይን ይሆንልሃል የሕይወት ምሰሶ ጣፋጭ የሚያፈራ፡፡


Tuesday, December 24, 2019

ቃሌን አጥፌያለሁ!

ውዴ ሆይ!

ቃል የገባሁትን ያኔ እንድንጋባ፣
ተሳስስበን ተሳስረን ቤት እንድንገነባ፣
የገባነውን ውል አጅቦን መሃላ፣
ትቼው ረስቼው ተካሁት በሌላ፤

ውድዬ ውዲቷ!

ለምን ሆነ ካልሽም ልብሽ ከታመመ ከገባሽ ትካዜ፣
ጥያቄ ከሆንሽ የቃሌ መታጠፍ ውሉን መሰረዜ፣
የኔ ማር!
የኔም ጥያቄ ነው ያንች የሆነው ሁሉ፣
የገመድ ቋጠሮ የተበተበ የማይገኝ ውሉ፣
መስቀለኛ መንገድ መሃሉ ላይ ጥሎ ድንግርግር አድራጊ፣
ሆኖብኛል እና ከግራ ወደቀኝ የሚያመላልሰኝ እንደዘሃ ዘጊ፣
በዋገምት የማይሽር ቁርባ ሠርቶብኝ ሕማምን ስቦብኝ ከነጥላ ወጊ፣
ነቀርሳ ሆኖብኝ ጣር ቢጠናብኝ እንጂ፣ ሌላ አልተካሁብሽም ፈጽመሽ አትስጊ፤

የኔ ውድ፣ ዓለሜ!

ዓለምን የሞላት ግሳንግሱ ሁሉ፣
አልጨበጥ ብሎ ቢጠፋብኝ ውሉ፣
ስለጋብቻችን ባስብ ባሰላስል ምን ብመታ መላ፣
በዛሬ አሻግሬ እያየሁ ሳወጣ ሳወርደው የነገን ሳሰላ፣
ነገ የሚያመጣው ያ ትንሹ ልጄ ያልተሟሸው ሸክላ፣
ሕማሙን ዐይቸው ተስፋዬ መንምኖ የእምነቴ ክር ላላ፤

እናልሽ የኔ ሆድ!

ላገባሽ ያልሁትን ቃሌን አጥፌያለሁ፣
ሐሳቤን ለውጬ ሌላ ሰው ሆኛለሁ፣
ጋብቻ አስጠልቶኝ ብቸኝነት ጥሞኝ ስላገኘሁ ለኔ፣
ሰመመን ውስጥ ነኝ ቀስቃሽ የማያሻኝ የሚሆን ከጎኔ፤

ስለዚህ ናፍቆቴ!

አልመጣም፣ ጋብቻችን ቀርቶ ውላችንም ፈርሷል፣
በጋራ ያቀድነው በኔ የግል ሕልም ከተተካ ከርሟል፤

ቢሆንም ግን ውዴ!

ማፍቀሬን አልክድም መወድድሽን አልረሳም፣ አይፋቅምና መቼም ቢሆን ከቶ፣
ስንቅ ስለሆነ የተመረገ ጠጅ፣ የመንፈሴ ቀለብ የጠጣሁት ጊዜ ትዝታው ተከፍቶ።

             ታመነ ቻላቸው
             14/04/2012

Wednesday, August 21, 2019

ገድለ እስከዚያው

         
"እኔ የተፈጠርኩት ሰዎችን ለማስከፋት ነው፤ ያስከፉኝን ለማስከፋት ነው፤ ፈጣሪንም ለማስከፋት ነው።" ይላሉ።  የነተበ ልብስ ለብሰው ጥንብዝ ብለው ሰክረው እየተንገዳገዱ ይራመዳሉ። ፊታቸው በማዲያት የተሸፈነ ነው። የፊታቸው ገጽታ ያሳለፉትን የጉስቁልና ዘመን ይተርካል።
"እስከዚያው ተመልከት እባላለሁ። የእያንዳንድሽን ገመና ፀሐይ ላይ አውጥቼ እንዳሰጣ ውክልና ያለኝ ብቸኛው ግለሰብ ነኝ" ይላሉ ምን ዓይነት ቀለም እንደነበራት እንኳን ለማወቅ በምታስቸግረው ኮዳቸው ከያዙት አረቄ እየተጎነጩ። አንዳንዴ የሚከተላቸው ግሪሳ አለ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ብቻቸውን መንተል መንተል ሲሉ ይታያሉ።
ወጣቶች፣ አዋቂዎችና ሽማግሌዎች ግን ይጠየፏቸዋል። ገና ድምጻቸውን "መጣ ደግሞ ይሄ ዓለም የረሳችው አምቡላም ሽማግሌ" ሲሉ ያማርራሉ። ይሄ ግን ለእስከዚያው ቁብ አይሰጣቸውም። "ያለበት ተጉላላበት"ን ይተርቱባቸዋል። "የረከሳችሁ ስለሆናችሁ፣ ያደፈ ማንነታችሁን ለመደበቅ በኔ ያደፈ ልብስ ታፌዛላችሁ። እድፋም ሁላ! ያደፈ ጭንቅላታችሁን ከቅርጭጭቱ አላቁት። ቅርጭጭታም ሁላ! ሃሃሃሃሃሃሃሃ!..." ይሉና ወንከር ወንከር እያሉትንሽ ይራመዳሉ።
ንግግራቸው ቢያሳርራቸውም ያሽካካሉ። እስኬው ሆዬ ዘውር ይሉና "ማክላላት ላህያ አመሉ ነው። የቀራችሁ መንከባለሉ ነው። ከዘዶቻችሁ የምትለዩት በሁለት እግር በመራመድ ብቻ ነው። በቀር ቁርጥ እነወሸን! ካካካካካካካካካ ....." ይሉና እርምጃቸውን ይጀምራሉ።
ደግሞ ተመልሰው በንዴት የጦዙትን ሰዎች ያሉ። እናም "እኔ የተፈጠርሁት ሰዎችን ለማስቀየም ነው። ፈጣሪንም ቢሆን!" ይላሉ። ተንደፋድፈው በጢማቸው ይደፋሉ። ትናንትም እንደዛሬው ነበሩ፤ ነገም እንደዚያው። ይሄው ነው የእስከዚያው ገድል ጉዞ።

Monday, February 11, 2019

መግባባት ይኖረን ዘንድ ምን እናድርግ? ምንስ እንሁን?

ከዐርባ አምስት (45) ዓመታት ቀደም ብሎ የጀመረው በሐገራዊ ጉዳዮቻችን ላይ የጋራ አቋም መያዝን ሽሽት ዛሬ ላይ የመጨረሻው ጫፍ ላይ ደርሷል። የአንድ ሐገር ሰዎች ተብለን እንጠራ እንጅ እርስ በእርስ የምንተያየው እንደተለያዩ ሐገራት ዜጎች ነው። እንደተለያዩ ሐገራት ብቻም ሳይሆን ታሪካዊ ጠላትነት እንዳላቸው ሐገራት ዜጎች መተያየት ከጀመርን ውለን አድረናል።

ኢትዮጵያ የሚለውን ሥም በጋራ እንጠራበት እንጂ ኢትዮጵያዊነትን በተመለከተ የምንጋራው አቋም የለንም። በአንድ ሐገር እየኖርን፣ አንድ የይለፍ ወረቀት (Pass Port) እየተጠቀምን፣ በአንድ መንግሥት ሥር እየተዳደርን፣ ወዘተ ... የጋራችን የምንለው እና የምንስማማበት ጉዳይ ግን የለንም። 

ይኸንን ከላይ ያነሳሁትን ነጥብ የሚያስረግጡ ብዙ ማሳያዎችን ማቅረብ ይቻላል። በርካታ የጥቁር ሕዝብ ሐገራትና ሕዝባቸው የነጻነት ፋና ወጊ አድርገው የሚያዩትን እና እንደድላቸው አድርገው የሚቆጥሩትን የዓድዋ ድል እንኳን ልንስማማበት አልቻልንም። የእነ እከሌ ድል ነው፤ የእኛ ጉዳይ አይደለም፤ ... ዓይነት የውርክብ ሐሳቦችን እየተወራወርን መናቆሪያ አድርገነዋል። ያለፈውን የኛው ታሪክ ከምንማርበት ይልቅ መበሻሸቂያ፣ መነቋቆሪያ፣ መነታረኪያ እነና የጥል ግንብ ማቆሚያ በማድረግ ላለመግባባት ስንኳትን እንውላለን።

ቋንቋን ከመግባቢያነትና ከሐሳብ መግለጫነት ነጥለን የጥልና የብጥብጥ መሣሪያ አድርገነዋል። በቋንቆቻችን ውስጥ የተከማቹ እውቀቶችን በመጋራትና በማጋራት የበሰለ ሐገራዊ አመለካከት ያለው ማኅበረሰብ ከመገንባት ይልቅ የመለያያ አጥር እየሠራንባቸው አቅጣጫው ወዳልታወቀ አድራሻ እየነጎድን ነው።  በቋንቆቻችን ውስጥ የተቀበሩ እውቀቶችን እያወጣን የጋራ የሚባል ማንነት ለመሥራት ከመጣር ይልቅ ልጆቻችን እና ታናናሾቻችን የማይግባቡበትን መንገድ ለመፍጠር የእነገሌን ቋንቋ ማወቅ የለባችሁም በማለት በእንቁላል ውስጥ እንዳለ ሽል አፍነን ለማስቀረት እንታትራለን። 

በዚህ ሁሉ ጉዟችን መግባባት የማይችል ዜጋ ለመፍጠር ተሳክቶልናል። ከተጣባን የችጋር ደከከን የሚያላቅቀን መንገድ መፈለግን ደግሞ በሚያስደምም ሁኔታ ረስተነዋል። የሰው ልጅ ያለውን በነጻነት የመሰብና የመሥራት ተፈጥሯዊ ሥጦታ በመንጠቅ ሲዋጣልን ራሳችንንም ሆነ ማኅበረሰባችንን የሚለውጥና ከድህነት አረንቋ የመምዘዣ መንገድ ለመቀየስ ግን ወገቡን እንደተመታ እባብ እየተቅመደመድን  ነው።

ለመሆኑ እንደዚህ የሆንነው ለምንድን ነው? ከዚህ የሐሳብ ድርቅና ቆፈንስ መውጣት የምንችለው እንዴትና በምን ዓይነት መንገድ ነው? መውጫ መንገዱን ለመፈለግስ ምን ማድረግና መሆን ይጠበቅብናል? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎች እያነሳን መወያየትና መሟገት አስፈላጊ ቢሆንም ረስተናቸዋል። በመሆኑም እንደግለሰብ የሚታየኝና የሚሰማኝን በዚኽች ጦማር በተከታታይ ለማቅረብ በመሞከር የድርሻየን ለመወጣት ጀምሬያለሁ። መግቢያው ይኼው። ቀጣዮቹ ክፍሎችም ይቀጥላሉ።

 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡