Thursday, October 4, 2018

ጠያቂዋም ተጠያቂውም ሥሙን እየጠሩት ያልተገለጠው የዐማራው የሕልውና ፈተና፡-


የLTV Show አዘጋጅ ቤተልሔም ታፈሰ እና የአ.ብ.ን ሊቀ መንበር ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ ያደረጉትን ሙግት መሰል ውይይት በጥሞና አዳመጥሁት፡፡ የዐማራው ማኅበረሰብ የሕልውና ፈተና ገጥሞታል የሚለው የንቅናቄው አቋም የተመላለሱት ጉዳይ ግልጽ ሊሆንልኝ አልቻለም፡፡ ጋዜጠኛዋ ትንኮሳ ትላለች፤ ሊቀ መንበሩ ደግሞ የህልውና ፈተና ይላሉ፡፡ የሕልውና ፈተና መሆኑን ለማስረዳት ብዙ ማስረጃዎችን መጥቀስ ይችሉ የነበረ ቢሆንም ረግጦ የማስረዳት ክፍተት አስተውየባቸዋለሁ፡፡ ጋዜጠኛዋም በበኩሏ የሕዝብ ቁጥር ብዛትን እየጠቀሰች ያህን ያህል ስፋት ያለው ማኅበረሰብ እንዴት የሕልውና ፈተና አለበት ሊባል ይችላል እያለች ትሞግታለች፡፡ ይህ ሁሉ አስፈላጊ ነበር ወይ የሚለው እንዳለ ሆኖ የሕልውና ፈተና ተጋርጦበታል ለሚለው ጉዳይ የሚከተሉትን አስረጂዎች ማየት ይቻላል፡፡
በዐማራው ሕዝብ ላይ የተጋረጠውን የህልውና አደጋ ተጋርጦበታል ሲባል፡-
1.  ዐማራው በተለያዩ ክልሎች ውስጥ ላለፉት ሠላሳ ዓመታት በጅምላ ሲገደል፣ ቤት ተዘግቶበት ሲቃጠል፣ ሲፋናቀልና ከርስቱ ሲነቀል የቆየ መሆኑ፤ አሁንም እነዚህ ጉዳዮች እየተፈጸሙ መሆናቸው፣
2.  የቤተሰብ ምጣኔን እንደሽፋን የዐማራ ወጣቶች መውለድ እንዳይችሉ የማድረግ ሥራዎች እየተሠሩ መሆናቸው፣
3.  ወንጀል ሳይኖርባቸው ዐማራ መሆናቸውና መብታቸውን በመጠየቃቸው ብቻ በየማጎሪያ ቤቱ እየሰበሰቡ እንዳይወልድ የማኮላሸት ሥራ እየተሠራበት መሆኑ፣
4.  የመንግሥት ሥርዓትን ከሚመሩ ድርጅቶች ጀምሮ በሐገሪቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች ዐማራን ጠላትና ጨቋኝ አድርጎ የመተረክና ይህንንም ለማስረጽ በተለያዩ መንገዶች እየተሠራ መሆኑ፣
5.  በኢኮኖሚ ሥርዓቱ ግፉእ እንዲሆን የማድረድ ተግባር በፖሊሲ ደረጃ ተቀርፆ የሚሠራበት መሆኑ፣
6.  ዐማራው በሐገሩ ማግኘት የሚገባውን ማግኘት እንዳይችል፤ ከማይምነት እንዳይላቀቅና በድኅነት ሲማቅቅ እንዲኖር እየተሠራበት መሆኑ፣
7.  በተለይም ጋዜጠኛዋ ራሷ የመከራከሪያ ነጥብ አድርጋ ለማሳመኛነት ያቀረበችው ጉዳይ ዐማራው ምን ያህል የህልውና ፈተና የገጠመው እንደሆነ ለማሳያነት የሚቀርብ እንጂ እሷ እንዳለችው የሕልውና ፈተና የሌለበት መሆኑን ሊያሳይ የሚችል አይደለም፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የዐማራውን ያህል በሥፋትና በከፍተኛ ሁኔታ ተሠራጭቶ የሚኖር ሌላ ማኅበረሰብ የለም፡፡ በየትኛውም የሀገሪቷ አካባቢዎች በጣም በርካታ ቁጥር ያላቸው አማሮች ይኖራሉ፡፡ በ2010 መስከረም ወር ላይ እን ኦቦ ለማ መገርሳ እንዳሉት በኦሮሚያ ክልል ብቻ እስከ 11, 000, 000 የሚደርሱ ዐማሮች ይገኛሉ፡፡ በሌሎች አካባቢዎችም ከዚህ የሚበልጥ ቁጥር ያለው ዐማራ አለ፡፡ ይሁን እንጂ በመንግሥት ደረጃ በታቀደና በታሰበበት መንገድ የዐማራውን ቁጥር የማሳነስ ሥራ ሲሠራ ኖሯል፡፡ ብዛቱ ከሐገሪቱ ሕዝብ እስከ 50% የሚሆነውን የመሚሸፍን ሆኖ እያለ በቁጥር ሁለተኛ እንደሆነ ፐሮፓጋንዳ መነዛቱ፣ በሕዝብና ቤት ቆጠራ ሪፖርትም የሕዝብ ቁጥሩ እየቀነሰ መሆኑ፣
8.  በተለያዩ የሐገሪቷ አካባቢዎች በሥፋት ተሠራጭቶ የሚኖረው ዐማራ ዐማራ ነኝ ሲል ከመንግሥት ሊያገኝ የሚገባውን ጥቅም የሚያስከለክለው በመሆኑ ምክንያት፣ ልጆቹ ቢማሩም ባይማሩም የሥራ እድል እናዳያገኙ የሚገደዱ በመሆናቸውም ምክንያት ዐማራነታቸውን ትተው በሌላ ብሔረሰብ ስም እየተመዘገቡ እንዲኖሩ እየተደረገ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡
በመሆኑም እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩ ምክንያቶች ዐማራው የሐገር አልባነት ስሜት እንዲሰማውና ተረጋግቶ ሕይወትን መምራት እንዳይችል የሚያደርጉ፤ በሕይወቱም ተስፈኛ እንዳይሆንና በሐገሩ እየተሳቀቀ እንዲኖር የሚያደርጉ ናቸው፡፡ ከዚህም በላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ የቁጥር መቀነስን እያመጡ የአናሳ ናችሁ እኛ ከናንተ የበለጠ ጥቅም ማግኘት ይገባናል የሚሉ ትረክቶች እንዲያቆጠቁጡ እያደረገ ነው፡፡ የሕልውና አደጋ (ፈተና) ሲባልም ሙሉ ለሙሉ የመውደም ጉዳይ ሳይሆን የነበረን መሠረት የማሳጣት፣ የማኅበረሰብን ሥነ ልቡና የማዳከምና በሐገሩ ጉዳይ አንገቱን ደፍቶ ሁሌም ተበዝባዥ አድርጎ የማስቀጠል ጉዳይን የሚመለከት ነው፡፡


Wednesday, October 3, 2018

ሁሉንም በግል መነጽራችን ማየት የአብሮነት ጉዟችን ፈተና



ያለፉት ዐርባ አምስት (45) ዓመታት የኢትዮጵያ ፖለቲካ በመጠላለፍና ጣት መቀሳሰር የተሞላ እንደነበርና እንደሆነ የሚያሳዩን በርካታ ማስረጃዎች አሉ፡፡ ይህም በዛሬው ትውልድ ላይ የቀረውን ጠባሳ ሰፊ እንዲሆንና ዐዲስና የለውጥ መሠረት የሚባለው ወጣት ሃይል በከንቱ እንዲቀር አድርጓል፣ ዛሬም እያደረገ ነው፡፡

በነዚህ ዓመታት እንደአሸን የፈሉት የፖለቲካ ድርጅቶች የፖለቲካቸውን መሠረት ያደረጉት በጨቋኝ ተጨቋኝ ትርክት ላይ በመሆኑና የነሱን የአሸዋ ላይ ውትወታ ተከትለው በነፋሱ አቅጣጫ በመመራት ታሪክ ጻፍን ያሉ ግለሰቦችም ንቅዘትን ለትውልድ የሚያስተላልፉ ትርጉም አልባና የቁርሾና የቂም ጎተራ የሆኑ ጥራዞችን አምርተዋል፡፡ በተለይ ደግሞ ከሁሉም በከፋ መልኩ ይህንን የፖለቲካና የታሪክ ዕይታ በሰፊው እያቀነቀነ የነበረው ድርጅት የመንግሥትነትን ሚና ከተቀበለ በኋላ የነበሩት ለሠላሳ ፈሪ ዓመታት መነጣልና መጠራጠር በከፍተኛ ሁኔታ ያጎነቆለባቸውና አሽቶም የጎመራባቸው ጊዜያት ናቸው፡፡

ሁሉም የኔ የሚለው ጎሣ ሥር ለመጠለልና ምክንያትና ተጠየቅን ጉድጓድ ምሶ ለመቅበር ሲንደፋደፍ ራሱንና መሠረታዊ ማንነቱ ሰብአዊነትን አጉብጧል፡፡ ሁሉም ነገሮች የሚመዘኑበት መንገድም ከምክንያትና ከተጠየቅ ይልቅ ከጎሣ እና ከቋንቋ ወገንተኝነት በማስተሳሰር ሆኗል፡፡ አንደአንድ ሐገር ዜጎች ከምናስብ ይልቅ እንደበርካታ ትንንሽ ሐገሮች በምንቆጥራቸው ጎሣዎቻችን ጥላ ሥር እንድንወሸቅ ሆነናል፡፡

የራሰችንን ዜጋ ሐገርህ አይደለም በማለት ማፈናቀል ከጀመርን በርከት ያሉ ዓመታት የተቆጠሩ ቢሆንም ያለፈው 2010 ዓ.ም እና የጀመርነው 2011 ዓ.ም ግን እጅግ የከፋው (ክፋቱ ከሚፈጸሙት አሰቃቂ ግድያዎች አንጻር ብቻ ሳይሆን ከነካቸው ጎሣዎች እና ከተፈናቀሉት ዜጎች ቁጥርም ጭምር ነው) ይመስለኛል፡፡ ይህንነ መፈናቀል የበለጠ የከፋ የሚያደርገው ደግሞ ከመፈናቀል በኋላ የሚደረጉ የድጋፍ እንቅስቃሴዎች እየታዩ ያለበት ዕይታና የሚሰጣቸው የፖለቲካ ወገንተኝነት ትርጉምም ነው፡፡

ሐገሩ ወደዚህ ምስቅልቅል እንዴት ገባች ብሎ ከሚጠይቀው ይልቅ ማን ለየትኛው ተፈናቃይ ድጋፍ አደረገ የሚለውን ጉዳይ እያሳደደ ድጋፍ አድራጊውን አካል በጎሣና የፖለቲካ ወገንተኝነት ከረጢት ውስጥ ለመክተት የሚሽቀዳደመው ወጣት ቁጥር በብዙ እጥፍ ይልቃል፡፡ አንድ ዓመት በማይሞላ ጊዜ ውስጥ ከ2,000,000 የሚበልጥ ቁጥር ያላቸው የሐገሩ ዜጎች ከኖሩበት ቀየ መፈናቀላቸውና መጎሳቆላቸው ከሚያሳዝነው ይልቅ የትኛው ዝነኛ ሰው ኬት አካባቢ ለተፈናቀሉ ሰዎች ድጋፍ አደረገ? የትኛው አክቲቪስት ከየትኛው አካባቢ የተፈናቀሉ ሰዎችን ጉዳይ አራገበ? የመሳሰሉ ጥያቄዎችን እያነሳ ሲያራግብና አቧራ ሲያጨስ የሚውለው ወጣት ቁጥር የትየለሌ ሆኗል፡፡

መፈናቀልን ማስቆም የሚቻልበትንና ተከባብሮና ተስማምቶ መኖር የሚቻልባቸው መንገዶችን ከሚፈልገው ኃይል ይልቅ እከሌ ከዚህ አካባቢ የተፈናቀሉ ሰዎችን የረዳው እንትን ለተባለው ብሔረሰብ ቀና አመለካከት ስለሌለው ነው፤ ከእንትን አካባቢ የተፈናቀሉት ሰዎች ድጋፍ ተዥጎድጉዶላቸው ከእንትን አካባቢ የተፈናቀሉትን ቀና ብሎ የሚያያቸው ጠፋ፤ ወዘተ የሚሉ ጉዳዮችን እያነሳ እየጣለ ጉንጭ አልፋ ሙግት ሲሟገት የሚውለው ይበልጣል፡፡

ከኔ ቤት ምን ክፍተት አለ? ከሌላውስ በኩል? መፍትሔውስ ምንድን ነው? የሚሉ መሠረታዊ ጥያቄዎችን እያነሳ ችግር የሚቀርፍ ሐሳብ ከመለዋወጥ ይልቅ ሁሉም ሰው እኔ ባየሁበት መንገድ ማየት ካልቻለ ጠላቴ ነው የሚል ፍረጃ ውስጥ ገብቶ ለመሸናነፍና ለመዋደቅ ደፋ ቀና ሲል የሚታይበት ሆኗል፡፡

ሆኖስ ግን፤ ሁሌም ሰው በተፈናቀለ ቁጥር እርዳታ በማሰባሰብ መፍትሔ ማምጣት ይቻላል ወይ? አንድ ጊዜ እርዳታ ያሰባሰበ ቡድን ወይም እርዳታ የለገሰ ግለሰብና ቡድንን በዚህ የነቀዘ የፖለቲካ ሥርዓት ምክንያት ሰዎች በተፈናቀሉ ቁጥር እርዳታ የመስጠት ግዴታ አለበት ወይ? እርዳታ ማድረግ ችግሩን መስቆም ይችላል ወይ? የፖለቲካ ሥርዓቱ በዚህ መንገድ ከቀጠለ የሚፈናቀለው ሰው ከማይፈናቀለው የሚበልጥበት ጊዜስ ሊመጣ አይችልም ወይ? ያለበት አካባቢ የሁል ጊዜ መኖሪያው እንደሆነ ተማምኖ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ዜጋስ ምን ይህል ነው?

በመጨረሻም ችግራችንን የበለጠ የሚያሰፉ ጉዳዮች ላይ እየተነታረክን የሚያቃቅሩን እና የበለጠ አደጋው የሚያሰፉ ጉዳዮች ላይ ተጠምደን ከምንውል መፍትሐየ ሊያመጡልን በሚችሉ ጉዳዮች ዙሪያ ሐሳብ እየተለዋወጥን የአብሮነት መንገዳችንን ብንጠርግ የተሸለ ይሆናል ብየ አስባለሁ፡፡

Thursday, June 22, 2017

ጎጃም ኑራ ማሬ (ክፍል 1)

(የዘፈኑ ‹ሙዚቃው› አጠቃላይ ሁኔታ)
የት ነበር ያኖርኩት ቀፎዬን ስል ኖሬ
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኑራ ማሬ፡፡
ብራናየ አንች የልጅነት ጓዴ
ተረሳሽ ወይ የሳቱ ዳር ተረት ባንዴ::

በዘብህ የተሰደደው ፍቅሩን (ሰብለወንጌል መሸሻን) ጎጃም አስቀምጦ ነው፡፡ ጎጃም ተስፋው አለች፡፡ ተስፋው ተከትላው መምጣት አልቻለችም፡፡ ትመጣለች ብሎ እየጠበቃት የውኃ ሽታ ሆና ስትቀርበት ፍቆት ሽታውን ሊፈልጋት ተመልሶ ወደ ጎጃም ጉዞ ጀመረ፡፡ የጎጃምን ምድር ዳርቻውን እንደረገጠ በሽፍቶች ተደብድቦ መራመድ እንኳን አቅቶት መንገድ ላይ ወድቆ አንዲት ሴት ታገኘውና ታስጠጋዋለች፡፡ በተጠጋበት ቤት ተስፋው ተቆራምዳ፣ መንኩሳ ቢጫ ልብስ ለብሳ ያገኛታል፡፡ በጣዕርና በሳቅ መሐል ሆኖ ሕይወቱ ታልፋለች፡፡

ይህ ፍቅር እስከመቃብር የተሰኘው ድንቅ መጽሐፍ የሚተርክልን ጉዳይ ነው፡፡ ይሀንን ነገር ቴዎድሮስ ካሳሁን በሙዚቃ ሰርቶ ሲያመጣልን ፍቅር እስከመቃብር የያዘው አድማስ ብቻ እንዲበቃው ሆኖ የቀረበ ሆኖ አይታየኝም፡፡ ይህንን እምነቴን ያስረዱልኝ ዘንድ ሁለት ነገሮችን እጠቅሳለሁ (ለጊዜው)፡፡

1.     1.  ዜማው፡- ሲጀምር ከቅዳሴ ዜማ ይነሳና ወደሚያስደልቅ ደማቅ የጎጃም ባሕላዊ ጭፈራ ምት ይሸጋገራል፡፡ ቅዳሴ በጎጃም ማኅበረሰብ ትልቅ ሥፍራ የሚሰጠው ከገበሬው እስከ ካህናቱ ቅዳሴ ቢታጎል መዓት የሚወርድባቸው፤ አምላካቸው ወደ ምድር መጥቶ ተሰቃይቶ የሚሞት የሚመስላቸው ናቸው፡፡ ቅዳሴ ከተጀመረ በኋላ ማንም እንዳይገባ የደጀ ሰላማቸውን በር ግጥም አድርገው ዘግተው በጥሞና የሚከታተሉ፣ በሩ ተከፍቶ ሰው ጥሶ ከገባ አካላቸው የተረገጠ ያህል ስቅቅ የሚላቸው፣ መላእክት ወደምድር መጥተው ለአምላካቸው እየሰገዱና እያሸበሸቡ እያለ ተረገጡ ብለው የሚያምኑ ናቸው፡፡ ሥለሆነም ዜማው በቅዳሴ መጀመሩ ስራው ማኅበረሰቡን በጥልቀት ከማየትና ከመረዳት የመነጨ መሆኑንና እጅግም በጥንቃቄ የተሠራ መሆኑን ያሳያል፡፡

ዜማው በቅዳሴ እንጀመረ በዚያው አይቀጥልም፡፡ አንጀት ወደሚበላ ነገር ግን ወደለቅሶ በሚመራ ደማቅ ዜማ ይሸጋገራል፡፡ ጎጃሞች የሚደልቁት ሲደሰቱ ብቻ አይደለም፤ ሲያዝኑም አንጂ፡፡ ጎጃሞች ሰው ሲሞት በየአድባሮቻቸው አደባባይ በመገኘት ሙሾ ያወርዳሉ፡፡ ሙሾው እጅግ ግጥም አዋቂነታቸው በተመሰከረላቸው  አስለቃሾች እየተመራ በረገዶ ታጅቦ በእናቶች ደረት ድቂ እየደመቀ የተለየ የሐዘን ስሜትን የሚፈጥር ዜማ ይፈጥራል፡፡ ዜማው እንጉርጉሮም ድለቃ የሚመስል ድምፀትም ያለው ነው፡፡ ይህ ድምፀት ነው በቴዎድሮስ ካሳሁን “ማር እስከ ጧፍ” ሙዚቃ ውስጥ የሚስተዋለው፡፡

ጎጃሞች በደስታቸው ወቅት መንደራቸው ምድርን በሚያንቀጠቅጥ ድለቃ ይቀልጣል፡፡ አዝመራ ከመሰብሰብ እስከሌሎች ማኅበራዊ ሁነቶች ባለው የእርስበርስ ግንኙነታቸው የደመቀ ጭፈራ ከመንደሮቻቸው አይጠፋም፡፡ ጧፍ ውስጥ የሚገኙት ቁጢቶች ሰም አስተባብሮ እንዳያያዛቸው ጎጃሞችን አጣምሮ የሚያያይዛቸውና ኑሯቸውን በሕብረት እንዲመሩ የሚያደርጋቸው ፍቅር ነው፡፡ ያ ፍቅራቸው ደግሞ የሚገለጸው ልብን በሚያሞቀው ዜማቸው ነው፡፡ ዜማ የሁሉ ነገራቸው መግለጫ መሣሪያ ነው፡፡ ዓይነቱ ይለያይ ይሆናል እንጂ፡፡

22. በግጥሙ ውስጥ የሚጠቀሱት ቃላት፡- በዚህ ሙዚቃ ግጥም ውስጥ ቴዎድሮስ ካሳሁን የተጠቀማቸው ቃላት እጅጉን ለጎጃምና ጎጃሜዎች የቀረቡ ናቸው፡፡ ይህም ከያኒው ሥራውን ለመሥራት ምን ይህል ስለማኅበረሰቡና ማኅበረሰቡ ላይ ትኩረቱን አድርጎ ስለተጻፈው ፍቅር እስከመቃብር መጽሐፍ በጽሞና አንዳሰላሰለ የሚያሳይ ነው፡፡ “የፀበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል” ይላል የዘፈኑ ግጥም ጀመሪያ ስንኝ፡፡ ፀበልና እንኮይ ከጎጃም ማኅበረሰብና ልጆች ጋር ከፍተኛ ትስስር ያላቸው ናቸው፡፡ ፀበል በጎጃም ማኅበረሰብ ዘንድ እጅግ የተከበረና ከማንኛውም ዓይነት የሕክምና ተግባር ቅድሚያ የሚሰጠው ፈውስ የማግኛ መንገድ ነው፡፡ እናም ከያኒው ሰብለወንጌልን ለመግለጽ የተጠቀመው፡፡

ኑራ-በተለመደው ዐማርኛ የሆነ ቦታ (ሥፍራ) ቆይታ የሚል ፍቺ አለው፡፡  ሌላ ተጨማሪ ፍቺም ይሸከማል፡፡ አንድም የሆነ ቦታ እያለች (ሳለች) ነው ለካ… የሚል፤ አንድም ለካ እሷ ናት እንደማለት፡፡ በቴዲ አፍሮ ዘፈን ተደጋግሞ የሚጠራው ቃልም “ጎጃም ኑራ ማሬ” የሚል ነው፡፡ ጎጃም “ጎጃም ኑራ ማሬ” ሲል አንድም በዛብህን የወከለው ሰው ሰብለ ወንጌልን ሸዋ ሲጠብቃት እሷ ግን ጎጃም ያች መሆኗን አመልካች ነው፡፡ አሊያም የኔ መድኃኒት ጎጃም ነች እንደማለትም አድርገን መውሰድ እንችላለን፡፡

ማር ከጣፋጭነቱ በተጨማሪ መድኃኒትነቱ ፍቱን የሆነ መሆኑ የታወቀ ሐቅ ነው፡፡ (ይቀጥላል-- ተጠናክሮ)


Thursday, June 8, 2017

ጎጃም ኑራ ማሬ (ተከታታይ ጽሑፍ)
መግቢያ
የጸበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል
ተሸፍና ዋርካ ከልሏት የዛፍ ጠል፤
ጸበል እንደማንኛውም ውኃ አይደለም፡፡ በውኃነቱ ውኃ ቢሆንም በግብሩና በክብሩ ግን የተለየ ነው፡፡ ያ ውኃ ያበቀላት እንኮይ ደግሞ የተቀደሰች ነች፡፡ ግጥም በትዕምርት የደመቀ ነውና ትዕምርታዊ ውክልናውን እያመሰጠሩ መጓዝ መጀመር ያለበት ከመጀመሪያዋ የግጥሙ መስመር ጀምሮ ነው፡፡ እንኮይ በጎጃም ወጣቶች ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነ ጣፋጭ ፍሬ ነው፡፡ የጣዕም መለኪያ ነው፡፡ በግጥሙ ውስጥ የቀረበችው እንኮይ ደግሞ የጸበል ዳር ነች፡፡ ማንም እንደፈለገ የማይነካት፤ የደረሰ ሁሉ የማይቀጥፋት፡፡ እንኮይዋ ሰብለወንጌል ነች፡፡ የንጹህ ዘር ከሚባለው የወቅቱ ማህበራዊ መዋቅር አካል ካንዱ የተወለደች፡፡ ማንም ቢፈልግ በቀላሉ የማያገኛት፤ በአጥር የተከበበች ግን በቅድስና የቀመጠች፡፡ ወንዙ በዙሪያዋ ያለው ተፈጥሮ ነው፡፡ ከምትበላው እስከምትጠጣው፣ ከምትለብሰው እስከምትቀመጥበት አቀማጥሎ የያዛት ማኅበረሰብ፡፡ ውበቷን ጠብቃ ደምቃ እንድትታይ ያደረጋት ማኅበረሰብ፡፡
ሁለተኛው ስንኝ ላይ ስንደርስ “ተሸፍና ዋርካ …” የሚል ሐረግ እናገኛለን፡፡ ዋርካ በኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ዘንድ ትልቅ፣ የተከበረ፣ … የሚባል ነገርን የሚወክል ግስም ያለው ዛፍ ነው፡፡ ዋርካ ሥር የሚበቅሉ ማናቸውም ዓይነት እጽዋት ወይ ኮስምነው ይቀራሉ፤ አሊያም ውበታቸው በዘርፋፋው የዋርካው ቅጠል ተከልሎ ማንም ሳያየው ይኖራል፡፡ የስንኙ ሁለተኛ ሐረግም የሚለው “… ከልሏት የዛፍ ጠል” አይደል፡፡ ዛፍ ተጠግቶ የወጣ ማናቸውም ተክል ቀጭጮ የሚቀር ነው፡፡ ኮስማና፡፡ እንደፈለገ ማደግም ሆነ መወዛወዝ የማይችል የትልቁ ዛፍ ጥገኛ ነው፡፡ ዛፉ ሲዘም አብሮ የሚዘም ዛፉ ጸጥ ሲል አብሮ ጸጥ የሚል በራሱ ትንፋሽ የማይንቀሳቀስ አሳዛኝ ተክል ይሆናል፡፡ ዛፉ ጨካኝ ከሆነ ድራሹ ይጠፋል፡፡ ሰብለወንጌልን የከለላት ዛፍ የወላጆቿ የጨዋ ዘር ነን፣ ከኛ የሚጋባ ከኛ የሚመጣጠን ጨዋ የጨዋ ልጅ እስካላገኘን ለማንም አንድርም የሚል፤ ከወደደችው ጋር ብትሔድ አስደፈረችን ብሎ ከሰውነት ወደዕቃነት አውርዶ የሚያስጥል ጎታች ማኅበራዊ እሳቤነው፡፡ ሰብለ በዚህ ጎታች አስተሳሰብ ምክንያት ውብ እያለች የጠወለገች፤ ኮኮብ እያለች ብርሃኗ የደበዘዘ ጉብልነች፡፡ ደማቋ ኮኮብ ሰብለ በተንሰራፋው ደንቃራ ማኅበራዊ ሥርዓት ምክንያት የተከደነች፤ መጫዎት ሲያምራት በትልቁ ዋርካ ተከልሎ ነፋስም ብርሃንም እንደተነፈገው ተክል ሁሉን የተከለከለች መንታላ ፍጡር፡፡
ቴዎድሮስ ካሳሁን በዚህ ሥራ ላይ መጠበቡ የጀመረው እንግዲህ ከመጀመሪያው የግጥሙ ስንኝ ከመጀመሪያው ሐረግ ጀምሮ ነው፡፡ እያንዳንዱ የዘፈኑ ግጥም ስንኞች ሐረግ ትዕምርት ያነገበ ነው፡፡ እያንዳንዱ ስንኝ መስመር በመስመር መተንተን የሚችል፡፡ እያንዳንዱ የግጥሙ አንጓ አንድ ትልቅ መጽሐፍ ሊወጣው የሚችል ትንታኔ የሚሠራበት በትዕምርት የተለወሰ ቋንቋ፡፡ እያንዳንዱ መስመርበ ቅመም ያበደ፡፡ እያንዳንዷ ቃል ተፈልቅቃ ስትዘረጋ ረጅም ርቀት መጓዝ የምትችልበት፡፡ በረቀቀ መንፈስ የረቀቀ፡፡ ሳስበው ሳስበው የዚህ ዘፈን ግጥም ሲጻፍ ቴዎድሮስ ብቻውን አይደለም፡፡ አንዳች የጥበብ ዛር እጁን ይዞ እየጎተተ እንደዚህ ብለህ ጻፍ እያለ ሲመራው የነበረ ይመስለኛል፡፡ እሱ ራሱ እንደተናገረው የዚህ ዘፈን ግጥም የተጻፈው በአንድ ምሽት ነው፡፡ ሆኖም ግን ይህ ሁሉ ትዕምርት የታጨቀበት ግጥም እንዲህ በቅጽበት በአንድ ምሽት ተጽፎ ይጠናቀቅ ዘንድ ምትኃታዊ መንፈስ ያስፈልጋል፡፡ ያ የመንፈስ ምትኃት ከቴዎድሮስ አእምሮ ስር ተወሽቆ እያንዳንዷን ቃል ከአርያም እየመዘዘ፤ እያንዳንዷን ሥንኝ በማር እየለወሰ እየጋተው ካልነበረ በስተቀር ይህንን አስማት አከል ግጥም በአንድ ምሽት በሰው አእምሮ መጻፍ እጅግ የሚከብድ አንዳንዴም የማይታሰብ ቢታሰብም በዚህ ዓይነት ነዛሪ መንፈስ ለብሶ ማቅረብ የመቻል ነገር አምላክ አከልነትን የሚጠይቅ ይመስለኛል፡፡
እንደኔ ቴዎድሮስ ካሳሁን የግጥም ችሎታው የመጠቀና የተመሳጠረ መሆኑን ለመመስከሁሉንም ዘፈኖቹን መስማት፣ አሊያም የዚህን ዘፈን ሙሉ ግጥም ማጣጣም የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ሁለት ስንኞች ብቻ ማስመስከሪያ ሊሆኑት ይችላሉ፡፡


Saturday, April 22, 2017

መውደድ ቢያደማኝም ….

ዐይንሽ ደምቆ የሚታየኝ ካረፍኩበት የሚጠቅሰኝ፣ የሚጠራኝ
ልቤ ባዶ፣ ዐይኔ ምኞት ስለያዘው መንፈሴን ስለራበኝ
እንጂማ
አንቺን እንድጠላሽ ከምውድሽ በላይ ነበረኝ ሰበቡ
ሕማም ቢሆንብኝ በደልን ማመንዠክ፣ ደጋግሞ ማሰቡ
እርም ይረመኝ ብየ አራግፌ ጣልኩት
አንቺን እንዳላጣ አምርሬ ጠላሁት
ታዲያስ
አንቺን ትቼ
ፍቅሬን ተጣልቼ
ውዴን ረስቼ
ፍቅርሽን ሸሽቼ
መግቢያዬ የት ሊሆን የትአባቴስ ልደርስ
ምንስ እያሸተትኩ ምንስ ልተነፍስ
መዓዛሽን ርቄ
መውደዴን ደፍቄ
ሳይሽ መደንበሩን መርበትበት መራዱን ለማን አቀብዬ
ብስክስክ ገላሽን ተሰባሪ መሳይ ወዴት አስቀምጬ ማን ይጠብቅ ብዬ፡፡

Sunday, November 27, 2016

ጥሩ መጽሐፍ ማንበብ

መጻሕፍት ጥሩ ሆነው ሲቀርቡ አእምሮን ያድሳሉ፡፡ የንባብ ፍላጎትን ከተወሸቀበት ሥርቻ  መንጥቀው ያወጡታል፡፡ በተለይማ በሕይወት ልምድ ታጅበው ሲቀርቡልን፡፡
የፕሮፈሰር ሽብሩ ተድላ "ከጉሬዛም ማርያም እስከ አዲስ አበባ፤ የሕይወት ጉዞና ትዝታየ" ምንም ዓይነት የተደበተ ስሜት ውስጥ ቢሆኑ የሚኮረኩር ነው፡፡ ከታሪካዊ መረጃዎች ሐብታምነቱ እስከ ባሕል መገለጫነቱ ይህ ነው በሚባል ዋጋ ሊተመን የሚችል አይደለም፡፡ ከኢትዮጵያ ማዕከላዊ አካባቢ ማኅበረሰብ አንዱ ከሆነው ከጎጃም ማኅበረሰብ ለማትተዋወቁ ያስተዋውቃችኋል፤ ለምትተዋወቁ ትውውቃችሁን ያደረጃል፡፡ ላደጋችሁበት ደግሞ የትዝታ መቆስቀሻ ይሆናልና አንብቡት፡፡

 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡