Thursday, June 8, 2017

ጎጃም ኑራ ማሬ (ተከታታይ ጽሑፍ)
መግቢያ
የጸበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል
ተሸፍና ዋርካ ከልሏት የዛፍ ጠል፤
ጸበል እንደማንኛውም ውኃ አይደለም፡፡ በውኃነቱ ውኃ ቢሆንም በግብሩና በክብሩ ግን የተለየ ነው፡፡ ያ ውኃ ያበቀላት እንኮይ ደግሞ የተቀደሰች ነች፡፡ ግጥም በትዕምርት የደመቀ ነውና ትዕምርታዊ ውክልናውን እያመሰጠሩ መጓዝ መጀመር ያለበት ከመጀመሪያዋ የግጥሙ መስመር ጀምሮ ነው፡፡ እንኮይ በጎጃም ወጣቶች ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነ ጣፋጭ ፍሬ ነው፡፡ የጣዕም መለኪያ ነው፡፡ በግጥሙ ውስጥ የቀረበችው እንኮይ ደግሞ የጸበል ዳር ነች፡፡ ማንም እንደፈለገ የማይነካት፤ የደረሰ ሁሉ የማይቀጥፋት፡፡ እንኮይዋ ሰብለወንጌል ነች፡፡ የንጹህ ዘር ከሚባለው የወቅቱ ማህበራዊ መዋቅር አካል ካንዱ የተወለደች፡፡ ማንም ቢፈልግ በቀላሉ የማያገኛት፤ በአጥር የተከበበች ግን በቅድስና የቀመጠች፡፡ ወንዙ በዙሪያዋ ያለው ተፈጥሮ ነው፡፡ ከምትበላው እስከምትጠጣው፣ ከምትለብሰው እስከምትቀመጥበት አቀማጥሎ የያዛት ማኅበረሰብ፡፡ ውበቷን ጠብቃ ደምቃ እንድትታይ ያደረጋት ማኅበረሰብ፡፡
ሁለተኛው ስንኝ ላይ ስንደርስ “ተሸፍና ዋርካ …” የሚል ሐረግ እናገኛለን፡፡ ዋርካ በኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ዘንድ ትልቅ፣ የተከበረ፣ … የሚባል ነገርን የሚወክል ግስም ያለው ዛፍ ነው፡፡ ዋርካ ሥር የሚበቅሉ ማናቸውም ዓይነት እጽዋት ወይ ኮስምነው ይቀራሉ፤ አሊያም ውበታቸው በዘርፋፋው የዋርካው ቅጠል ተከልሎ ማንም ሳያየው ይኖራል፡፡ የስንኙ ሁለተኛ ሐረግም የሚለው “… ከልሏት የዛፍ ጠል” አይደል፡፡ ዛፍ ተጠግቶ የወጣ ማናቸውም ተክል ቀጭጮ የሚቀር ነው፡፡ ኮስማና፡፡ እንደፈለገ ማደግም ሆነ መወዛወዝ የማይችል የትልቁ ዛፍ ጥገኛ ነው፡፡ ዛፉ ሲዘም አብሮ የሚዘም ዛፉ ጸጥ ሲል አብሮ ጸጥ የሚል በራሱ ትንፋሽ የማይንቀሳቀስ አሳዛኝ ተክል ይሆናል፡፡ ዛፉ ጨካኝ ከሆነ ድራሹ ይጠፋል፡፡ ሰብለወንጌልን የከለላት ዛፍ የወላጆቿ የጨዋ ዘር ነን፣ ከኛ የሚጋባ ከኛ የሚመጣጠን ጨዋ የጨዋ ልጅ እስካላገኘን ለማንም አንድርም የሚል፤ ከወደደችው ጋር ብትሔድ አስደፈረችን ብሎ ከሰውነት ወደዕቃነት አውርዶ የሚያስጥል ጎታች ማኅበራዊ እሳቤነው፡፡ ሰብለ በዚህ ጎታች አስተሳሰብ ምክንያት ውብ እያለች የጠወለገች፤ ኮኮብ እያለች ብርሃኗ የደበዘዘ ጉብልነች፡፡ ደማቋ ኮኮብ ሰብለ በተንሰራፋው ደንቃራ ማኅበራዊ ሥርዓት ምክንያት የተከደነች፤ መጫዎት ሲያምራት በትልቁ ዋርካ ተከልሎ ነፋስም ብርሃንም እንደተነፈገው ተክል ሁሉን የተከለከለች መንታላ ፍጡር፡፡
ቴዎድሮስ ካሳሁን በዚህ ሥራ ላይ መጠበቡ የጀመረው እንግዲህ ከመጀመሪያው የግጥሙ ስንኝ ከመጀመሪያው ሐረግ ጀምሮ ነው፡፡ እያንዳንዱ የዘፈኑ ግጥም ስንኞች ሐረግ ትዕምርት ያነገበ ነው፡፡ እያንዳንዱ ስንኝ መስመር በመስመር መተንተን የሚችል፡፡ እያንዳንዱ የግጥሙ አንጓ አንድ ትልቅ መጽሐፍ ሊወጣው የሚችል ትንታኔ የሚሠራበት በትዕምርት የተለወሰ ቋንቋ፡፡ እያንዳንዱ መስመርበ ቅመም ያበደ፡፡ እያንዳንዷ ቃል ተፈልቅቃ ስትዘረጋ ረጅም ርቀት መጓዝ የምትችልበት፡፡ በረቀቀ መንፈስ የረቀቀ፡፡ ሳስበው ሳስበው የዚህ ዘፈን ግጥም ሲጻፍ ቴዎድሮስ ብቻውን አይደለም፡፡ አንዳች የጥበብ ዛር እጁን ይዞ እየጎተተ እንደዚህ ብለህ ጻፍ እያለ ሲመራው የነበረ ይመስለኛል፡፡ እሱ ራሱ እንደተናገረው የዚህ ዘፈን ግጥም የተጻፈው በአንድ ምሽት ነው፡፡ ሆኖም ግን ይህ ሁሉ ትዕምርት የታጨቀበት ግጥም እንዲህ በቅጽበት በአንድ ምሽት ተጽፎ ይጠናቀቅ ዘንድ ምትኃታዊ መንፈስ ያስፈልጋል፡፡ ያ የመንፈስ ምትኃት ከቴዎድሮስ አእምሮ ስር ተወሽቆ እያንዳንዷን ቃል ከአርያም እየመዘዘ፤ እያንዳንዷን ሥንኝ በማር እየለወሰ እየጋተው ካልነበረ በስተቀር ይህንን አስማት አከል ግጥም በአንድ ምሽት በሰው አእምሮ መጻፍ እጅግ የሚከብድ አንዳንዴም የማይታሰብ ቢታሰብም በዚህ ዓይነት ነዛሪ መንፈስ ለብሶ ማቅረብ የመቻል ነገር አምላክ አከልነትን የሚጠይቅ ይመስለኛል፡፡
እንደኔ ቴዎድሮስ ካሳሁን የግጥም ችሎታው የመጠቀና የተመሳጠረ መሆኑን ለመመስከሁሉንም ዘፈኖቹን መስማት፣ አሊያም የዚህን ዘፈን ሙሉ ግጥም ማጣጣም የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ሁለት ስንኞች ብቻ ማስመስከሪያ ሊሆኑት ይችላሉ፡፡


No comments:

 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡