Thursday, June 22, 2017

ጎጃም ኑራ ማሬ (ክፍል 1)

(የዘፈኑ ‹ሙዚቃው› አጠቃላይ ሁኔታ)
የት ነበር ያኖርኩት ቀፎዬን ስል ኖሬ
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኑራ ማሬ፡፡
ብራናየ አንች የልጅነት ጓዴ
ተረሳሽ ወይ የሳቱ ዳር ተረት ባንዴ::

በዘብህ የተሰደደው ፍቅሩን (ሰብለወንጌል መሸሻን) ጎጃም አስቀምጦ ነው፡፡ ጎጃም ተስፋው አለች፡፡ ተስፋው ተከትላው መምጣት አልቻለችም፡፡ ትመጣለች ብሎ እየጠበቃት የውኃ ሽታ ሆና ስትቀርበት ፍቆት ሽታውን ሊፈልጋት ተመልሶ ወደ ጎጃም ጉዞ ጀመረ፡፡ የጎጃምን ምድር ዳርቻውን እንደረገጠ በሽፍቶች ተደብድቦ መራመድ እንኳን አቅቶት መንገድ ላይ ወድቆ አንዲት ሴት ታገኘውና ታስጠጋዋለች፡፡ በተጠጋበት ቤት ተስፋው ተቆራምዳ፣ መንኩሳ ቢጫ ልብስ ለብሳ ያገኛታል፡፡ በጣዕርና በሳቅ መሐል ሆኖ ሕይወቱ ታልፋለች፡፡

ይህ ፍቅር እስከመቃብር የተሰኘው ድንቅ መጽሐፍ የሚተርክልን ጉዳይ ነው፡፡ ይሀንን ነገር ቴዎድሮስ ካሳሁን በሙዚቃ ሰርቶ ሲያመጣልን ፍቅር እስከመቃብር የያዘው አድማስ ብቻ እንዲበቃው ሆኖ የቀረበ ሆኖ አይታየኝም፡፡ ይህንን እምነቴን ያስረዱልኝ ዘንድ ሁለት ነገሮችን እጠቅሳለሁ (ለጊዜው)፡፡

1.     1.  ዜማው፡- ሲጀምር ከቅዳሴ ዜማ ይነሳና ወደሚያስደልቅ ደማቅ የጎጃም ባሕላዊ ጭፈራ ምት ይሸጋገራል፡፡ ቅዳሴ በጎጃም ማኅበረሰብ ትልቅ ሥፍራ የሚሰጠው ከገበሬው እስከ ካህናቱ ቅዳሴ ቢታጎል መዓት የሚወርድባቸው፤ አምላካቸው ወደ ምድር መጥቶ ተሰቃይቶ የሚሞት የሚመስላቸው ናቸው፡፡ ቅዳሴ ከተጀመረ በኋላ ማንም እንዳይገባ የደጀ ሰላማቸውን በር ግጥም አድርገው ዘግተው በጥሞና የሚከታተሉ፣ በሩ ተከፍቶ ሰው ጥሶ ከገባ አካላቸው የተረገጠ ያህል ስቅቅ የሚላቸው፣ መላእክት ወደምድር መጥተው ለአምላካቸው እየሰገዱና እያሸበሸቡ እያለ ተረገጡ ብለው የሚያምኑ ናቸው፡፡ ሥለሆነም ዜማው በቅዳሴ መጀመሩ ስራው ማኅበረሰቡን በጥልቀት ከማየትና ከመረዳት የመነጨ መሆኑንና እጅግም በጥንቃቄ የተሠራ መሆኑን ያሳያል፡፡

ዜማው በቅዳሴ እንጀመረ በዚያው አይቀጥልም፡፡ አንጀት ወደሚበላ ነገር ግን ወደለቅሶ በሚመራ ደማቅ ዜማ ይሸጋገራል፡፡ ጎጃሞች የሚደልቁት ሲደሰቱ ብቻ አይደለም፤ ሲያዝኑም አንጂ፡፡ ጎጃሞች ሰው ሲሞት በየአድባሮቻቸው አደባባይ በመገኘት ሙሾ ያወርዳሉ፡፡ ሙሾው እጅግ ግጥም አዋቂነታቸው በተመሰከረላቸው  አስለቃሾች እየተመራ በረገዶ ታጅቦ በእናቶች ደረት ድቂ እየደመቀ የተለየ የሐዘን ስሜትን የሚፈጥር ዜማ ይፈጥራል፡፡ ዜማው እንጉርጉሮም ድለቃ የሚመስል ድምፀትም ያለው ነው፡፡ ይህ ድምፀት ነው በቴዎድሮስ ካሳሁን “ማር እስከ ጧፍ” ሙዚቃ ውስጥ የሚስተዋለው፡፡

ጎጃሞች በደስታቸው ወቅት መንደራቸው ምድርን በሚያንቀጠቅጥ ድለቃ ይቀልጣል፡፡ አዝመራ ከመሰብሰብ እስከሌሎች ማኅበራዊ ሁነቶች ባለው የእርስበርስ ግንኙነታቸው የደመቀ ጭፈራ ከመንደሮቻቸው አይጠፋም፡፡ ጧፍ ውስጥ የሚገኙት ቁጢቶች ሰም አስተባብሮ እንዳያያዛቸው ጎጃሞችን አጣምሮ የሚያያይዛቸውና ኑሯቸውን በሕብረት እንዲመሩ የሚያደርጋቸው ፍቅር ነው፡፡ ያ ፍቅራቸው ደግሞ የሚገለጸው ልብን በሚያሞቀው ዜማቸው ነው፡፡ ዜማ የሁሉ ነገራቸው መግለጫ መሣሪያ ነው፡፡ ዓይነቱ ይለያይ ይሆናል እንጂ፡፡

22. በግጥሙ ውስጥ የሚጠቀሱት ቃላት፡- በዚህ ሙዚቃ ግጥም ውስጥ ቴዎድሮስ ካሳሁን የተጠቀማቸው ቃላት እጅጉን ለጎጃምና ጎጃሜዎች የቀረቡ ናቸው፡፡ ይህም ከያኒው ሥራውን ለመሥራት ምን ይህል ስለማኅበረሰቡና ማኅበረሰቡ ላይ ትኩረቱን አድርጎ ስለተጻፈው ፍቅር እስከመቃብር መጽሐፍ በጽሞና አንዳሰላሰለ የሚያሳይ ነው፡፡ “የፀበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል” ይላል የዘፈኑ ግጥም ጀመሪያ ስንኝ፡፡ ፀበልና እንኮይ ከጎጃም ማኅበረሰብና ልጆች ጋር ከፍተኛ ትስስር ያላቸው ናቸው፡፡ ፀበል በጎጃም ማኅበረሰብ ዘንድ እጅግ የተከበረና ከማንኛውም ዓይነት የሕክምና ተግባር ቅድሚያ የሚሰጠው ፈውስ የማግኛ መንገድ ነው፡፡ እናም ከያኒው ሰብለወንጌልን ለመግለጽ የተጠቀመው፡፡

ኑራ-በተለመደው ዐማርኛ የሆነ ቦታ (ሥፍራ) ቆይታ የሚል ፍቺ አለው፡፡  ሌላ ተጨማሪ ፍቺም ይሸከማል፡፡ አንድም የሆነ ቦታ እያለች (ሳለች) ነው ለካ… የሚል፤ አንድም ለካ እሷ ናት እንደማለት፡፡ በቴዲ አፍሮ ዘፈን ተደጋግሞ የሚጠራው ቃልም “ጎጃም ኑራ ማሬ” የሚል ነው፡፡ ጎጃም “ጎጃም ኑራ ማሬ” ሲል አንድም በዛብህን የወከለው ሰው ሰብለ ወንጌልን ሸዋ ሲጠብቃት እሷ ግን ጎጃም ያች መሆኗን አመልካች ነው፡፡ አሊያም የኔ መድኃኒት ጎጃም ነች እንደማለትም አድርገን መውሰድ እንችላለን፡፡

ማር ከጣፋጭነቱ በተጨማሪ መድኃኒትነቱ ፍቱን የሆነ መሆኑ የታወቀ ሐቅ ነው፡፡ (ይቀጥላል-- ተጠናክሮ)


Thursday, June 8, 2017

ጎጃም ኑራ ማሬ (ተከታታይ ጽሑፍ)
መግቢያ
የጸበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል
ተሸፍና ዋርካ ከልሏት የዛፍ ጠል፤
ጸበል እንደማንኛውም ውኃ አይደለም፡፡ በውኃነቱ ውኃ ቢሆንም በግብሩና በክብሩ ግን የተለየ ነው፡፡ ያ ውኃ ያበቀላት እንኮይ ደግሞ የተቀደሰች ነች፡፡ ግጥም በትዕምርት የደመቀ ነውና ትዕምርታዊ ውክልናውን እያመሰጠሩ መጓዝ መጀመር ያለበት ከመጀመሪያዋ የግጥሙ መስመር ጀምሮ ነው፡፡ እንኮይ በጎጃም ወጣቶች ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነ ጣፋጭ ፍሬ ነው፡፡ የጣዕም መለኪያ ነው፡፡ በግጥሙ ውስጥ የቀረበችው እንኮይ ደግሞ የጸበል ዳር ነች፡፡ ማንም እንደፈለገ የማይነካት፤ የደረሰ ሁሉ የማይቀጥፋት፡፡ እንኮይዋ ሰብለወንጌል ነች፡፡ የንጹህ ዘር ከሚባለው የወቅቱ ማህበራዊ መዋቅር አካል ካንዱ የተወለደች፡፡ ማንም ቢፈልግ በቀላሉ የማያገኛት፤ በአጥር የተከበበች ግን በቅድስና የቀመጠች፡፡ ወንዙ በዙሪያዋ ያለው ተፈጥሮ ነው፡፡ ከምትበላው እስከምትጠጣው፣ ከምትለብሰው እስከምትቀመጥበት አቀማጥሎ የያዛት ማኅበረሰብ፡፡ ውበቷን ጠብቃ ደምቃ እንድትታይ ያደረጋት ማኅበረሰብ፡፡
ሁለተኛው ስንኝ ላይ ስንደርስ “ተሸፍና ዋርካ …” የሚል ሐረግ እናገኛለን፡፡ ዋርካ በኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ዘንድ ትልቅ፣ የተከበረ፣ … የሚባል ነገርን የሚወክል ግስም ያለው ዛፍ ነው፡፡ ዋርካ ሥር የሚበቅሉ ማናቸውም ዓይነት እጽዋት ወይ ኮስምነው ይቀራሉ፤ አሊያም ውበታቸው በዘርፋፋው የዋርካው ቅጠል ተከልሎ ማንም ሳያየው ይኖራል፡፡ የስንኙ ሁለተኛ ሐረግም የሚለው “… ከልሏት የዛፍ ጠል” አይደል፡፡ ዛፍ ተጠግቶ የወጣ ማናቸውም ተክል ቀጭጮ የሚቀር ነው፡፡ ኮስማና፡፡ እንደፈለገ ማደግም ሆነ መወዛወዝ የማይችል የትልቁ ዛፍ ጥገኛ ነው፡፡ ዛፉ ሲዘም አብሮ የሚዘም ዛፉ ጸጥ ሲል አብሮ ጸጥ የሚል በራሱ ትንፋሽ የማይንቀሳቀስ አሳዛኝ ተክል ይሆናል፡፡ ዛፉ ጨካኝ ከሆነ ድራሹ ይጠፋል፡፡ ሰብለወንጌልን የከለላት ዛፍ የወላጆቿ የጨዋ ዘር ነን፣ ከኛ የሚጋባ ከኛ የሚመጣጠን ጨዋ የጨዋ ልጅ እስካላገኘን ለማንም አንድርም የሚል፤ ከወደደችው ጋር ብትሔድ አስደፈረችን ብሎ ከሰውነት ወደዕቃነት አውርዶ የሚያስጥል ጎታች ማኅበራዊ እሳቤነው፡፡ ሰብለ በዚህ ጎታች አስተሳሰብ ምክንያት ውብ እያለች የጠወለገች፤ ኮኮብ እያለች ብርሃኗ የደበዘዘ ጉብልነች፡፡ ደማቋ ኮኮብ ሰብለ በተንሰራፋው ደንቃራ ማኅበራዊ ሥርዓት ምክንያት የተከደነች፤ መጫዎት ሲያምራት በትልቁ ዋርካ ተከልሎ ነፋስም ብርሃንም እንደተነፈገው ተክል ሁሉን የተከለከለች መንታላ ፍጡር፡፡
ቴዎድሮስ ካሳሁን በዚህ ሥራ ላይ መጠበቡ የጀመረው እንግዲህ ከመጀመሪያው የግጥሙ ስንኝ ከመጀመሪያው ሐረግ ጀምሮ ነው፡፡ እያንዳንዱ የዘፈኑ ግጥም ስንኞች ሐረግ ትዕምርት ያነገበ ነው፡፡ እያንዳንዱ ስንኝ መስመር በመስመር መተንተን የሚችል፡፡ እያንዳንዱ የግጥሙ አንጓ አንድ ትልቅ መጽሐፍ ሊወጣው የሚችል ትንታኔ የሚሠራበት በትዕምርት የተለወሰ ቋንቋ፡፡ እያንዳንዱ መስመርበ ቅመም ያበደ፡፡ እያንዳንዷ ቃል ተፈልቅቃ ስትዘረጋ ረጅም ርቀት መጓዝ የምትችልበት፡፡ በረቀቀ መንፈስ የረቀቀ፡፡ ሳስበው ሳስበው የዚህ ዘፈን ግጥም ሲጻፍ ቴዎድሮስ ብቻውን አይደለም፡፡ አንዳች የጥበብ ዛር እጁን ይዞ እየጎተተ እንደዚህ ብለህ ጻፍ እያለ ሲመራው የነበረ ይመስለኛል፡፡ እሱ ራሱ እንደተናገረው የዚህ ዘፈን ግጥም የተጻፈው በአንድ ምሽት ነው፡፡ ሆኖም ግን ይህ ሁሉ ትዕምርት የታጨቀበት ግጥም እንዲህ በቅጽበት በአንድ ምሽት ተጽፎ ይጠናቀቅ ዘንድ ምትኃታዊ መንፈስ ያስፈልጋል፡፡ ያ የመንፈስ ምትኃት ከቴዎድሮስ አእምሮ ስር ተወሽቆ እያንዳንዷን ቃል ከአርያም እየመዘዘ፤ እያንዳንዷን ሥንኝ በማር እየለወሰ እየጋተው ካልነበረ በስተቀር ይህንን አስማት አከል ግጥም በአንድ ምሽት በሰው አእምሮ መጻፍ እጅግ የሚከብድ አንዳንዴም የማይታሰብ ቢታሰብም በዚህ ዓይነት ነዛሪ መንፈስ ለብሶ ማቅረብ የመቻል ነገር አምላክ አከልነትን የሚጠይቅ ይመስለኛል፡፡
እንደኔ ቴዎድሮስ ካሳሁን የግጥም ችሎታው የመጠቀና የተመሳጠረ መሆኑን ለመመስከሁሉንም ዘፈኖቹን መስማት፣ አሊያም የዚህን ዘፈን ሙሉ ግጥም ማጣጣም የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ሁለት ስንኞች ብቻ ማስመስከሪያ ሊሆኑት ይችላሉ፡፡


Saturday, April 22, 2017

መውደድ ቢያደማኝም ….

ዐይንሽ ደምቆ የሚታየኝ ካረፍኩበት የሚጠቅሰኝ፣ የሚጠራኝ
ልቤ ባዶ፣ ዐይኔ ምኞት ስለያዘው መንፈሴን ስለራበኝ
እንጂማ
አንቺን እንድጠላሽ ከምውድሽ በላይ ነበረኝ ሰበቡ
ሕማም ቢሆንብኝ በደልን ማመንዠክ፣ ደጋግሞ ማሰቡ
እርም ይረመኝ ብየ አራግፌ ጣልኩት
አንቺን እንዳላጣ አምርሬ ጠላሁት
ታዲያስ
አንቺን ትቼ
ፍቅሬን ተጣልቼ
ውዴን ረስቼ
ፍቅርሽን ሸሽቼ
መግቢያዬ የት ሊሆን የትአባቴስ ልደርስ
ምንስ እያሸተትኩ ምንስ ልተነፍስ
መዓዛሽን ርቄ
መውደዴን ደፍቄ
ሳይሽ መደንበሩን መርበትበት መራዱን ለማን አቀብዬ
ብስክስክ ገላሽን ተሰባሪ መሳይ ወዴት አስቀምጬ ማን ይጠብቅ ብዬ፡፡

 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡