Monday, September 18, 2023

አይቀርም ተኝቶ

 እንኳን ነፋስ መንፈስ

ውቅያኖስ ቢመጣ በመዓበል ታጀቦ
ውሽንፍሩን ይዞ ወጀብ አሰክተሎ፤
መውደዱን ረግጦት አፈርን አልብሶ
ሌላ የሚያስገባ በር ሰጥቶ ለጀቦ
ድፍን ልብ የለኝም የሚቀር ተታልሎ፡፡
All reactions:

Friday, July 16, 2021

ከወዴት ሊመጣ …?


ገና በማለዳ ለማኙ ሳያ* ወፍም ሳይንጫጫ ቀድሞ ከንጋቱ፣
ነቅቶ የሚያነቃን ውርጭ ሳይቆልፈው ስል ሆኖ አንደበቱ፣
“ማን ይሆን ዘነድሮን የሚገኘው አልፎ፤
ከመዓት ከመከራው ከመቅሰፍቱ ተርፎ”
እያንጎራጎረ ሲያዜም እየሰማን ከንፈር እየመጠጥን፣
ሥም ያወጣንለት መጠሪያ ‘ሚሆነው “እብድ ወፈፌ” ብለን፣
መንጋቱ ‘ሚታወቅ ሰማይ መገለጡ ጨለማው ማለፉ፣
በእሱው ዜማ ነበር ሁሌ ‘ሚታወጁ ሰርክ የሚለፈፉ፣
በእሱ እንዳልነበረ ደምቆ የምናየው ተውቦ መንገዱ፣
የተሳለቅንበት ጆሮ የነሳነው የምንለው እብዱ፤
ዛሬ፡-
በተራችን ሁላችንም አብደን ሲጠፋብን መላ፣
እህል እየጠጣን ውኃ ልናላምጥ አኝከን ልንበላ፣
ነፋስም ልንጨብጥ ስናባዝን ስንለፋ፣
ውቅያኖስን ልንጠልቅ ጨርሰን በጭልፋ፣
ዳናው ቢናፍቀን ቢያምረን እንጉርጉሮው፣
ማን አየሁ ሊለን ምን ጅብ እንደበላው?
እናማ
ዜማውን ተውሰን ሥንኝ አሰናኝተን፣
እንዲህ ያለ ለቅሶ እንጉርጉሮ አወጣን፣
ዛሬስ ወዴት ገብቶ ምን ጅብ ቢውጠው ነው ዳናውን ያጠፋ፣
አፋችንን ሆኖ የማይናገረው ምን ሆነን እንዲያይ ነው ካሁኑ የከፋ፣
“ማን ይሆን …” እያለ አይናገር ምነው የማይጮኸው ዛሬ፣
ግድግዳው ተንዶ መጠጊያ ስናጣ ስንከበብ በአውሬ፣

Thursday, August 27, 2020

ማንም ነህ ምንም ነህ (2)

ምናምኒት ነገር እጅህ ላይ ባይገኝ ብታጣ ብትነጣ፣

እሳት ተለቅቆብህ ከቤት ብትሳደድ ሜዳ ብትሰጣ፣

አዝመራህም ነድዶ ጨገሬታ ጠፍቶ ጠኔህም ቢበዛ፣

ዕድል ፊት ብተነሳህ አሳዳጅ የሚሆን ተላትህን ብትገዛ፣

አይክፋህ ወንድሜ፣

በደል አይሰማህ መገፋት መጣልህ ፈፅሞ አያስከፋህ፤

ምክንያቱም፣

አንተ ማለት ለዓለም "ምንም ነህ ማንም ነህ"

 

ወገኔ ነው ያልኸው እምነት ጥለህበት ያደረግኸው ተስፋ፣

ቢሸሽ ቢሸሸግም ርቆ እየሔደ ካይንህ ተተሰውሮ ከጎንህ ቢጠፋ፣

ጊዜ እየታከከ ጉልበት ቢያጎለብት ለውድቀትህ ቢቆም አንተኑ ሊገፋ፣

ብንን ብሎ ቢሔድ ነፋስ እንደገፋው እንደጉም ቀሎ የጣልህበት ተስፋ፣

አይክፋህ ወንድሜ፣

በደል አይሰማህ መገፋት መጣልህ ፈፅሞ አያስከፋህ፤

ምክንያቱም፣

አንተ ማለት ለዓለም "ምንም ነህ ማንም ነህ"

 

የምትገብርለት ዓመት እየጠበቅህ፣

ቆሜያለሁ የሚልህ አንተን ልጠብቅህ፣

ካጥቂዎችህ ቢያብር ደጋግሞ ቢክድህ፣

ዓለም ስለተወህ ዓለም ስለረሳህ፣

አይክፋህ ወንድሜ በደል አይሰማህ፣

 

ይልቅስ፣

ቅስምህን አበርታ መንፈስህን አጽና፣

ቀበቶህን አጥብቅ አንገትህንም አቅና፣

አንተን የሚታደግ አውጪ ከፈተና፣

ከራሥህ በስተቀር ማንም የለምና፤

 

አልያማ፣

ጥረህ ተጣጥረህ ታግለህ ካላሸነፍህ ካልወጣህ አርነት፣

ዝምታህ ብርታቱ መታገስህ ኃይል ሆኖት ጉልበት፣

ሽህ ምንተሸህ ሆኖ ተንጋግቶ ይመጣል፣

የቅስምህ መሰበር ውስጡን ወኔ ሞልቶት፣

ኪሱን ሊያደላድል ሊሞላው የሱን ቤት፣

ትርፉን እያሰላ ሊሸጥ ያንተን ሕይወት፣

ምክንያቱም፣

ራሥህ ለራሥህ መድኃኒት ካልሆንኸው መንፈስህ በርትቶ፣

ደድረህ ካልመከትህ ኃይልህ ተጠራቅሞ ቅስምህም ጎልብቶ፣

ዓለም አይሰማህም ደራሽም የለህም፣

የሚገፋህ እንጂ ደጋፊ አታገኝም፡፡

 እኔ የማወራት የእርሷ ጆሮ ሲደርስ መልኩን እየሳተ እየተቀየረ፣ ከማፋቀር ይልቅ እኛን ከማዋደድ ጥል ፈጣሪ ኾነን እያጠራጠረ፡፡